«የፊልም ባለሞያዎች ዝርዝርን በአማርኛ ለመጻፍ የመረጥኩበት ምክንያት፤ አማርኛ እጅግ ጥንታዊ ከሆኑ የዓለማችን የጽሑፍ ቋንቋዎች አንዱ በመሆኑ ነው። በዓለም እንዲህ ዓይነት ቋንቋዎች ጥቂት ናቸው። ይህ ውብ ፊደላት ያሉት ቋንቋ በኢትዮጵያና በጥቂት ሰዎች በኤርትራ ይነገራል።»
ኒዤራዊቷ ጸሐፊና የፊልም ዳይሬክተር ራማቱ ኪየታ፣ በእንግሊዝኛ “The wedding ring” በአማርኛ «የጋብቻ ቀለበቱ» በምዕራብ አፍሪካ አገሮች በሚነገረው የሐውሳ ቋንቋ «ዝናሪያ» ያለችው ፊልሟ በቅርቡ በአምስተርዳም ዓለም አቀፍ የፊልም ፌስቲቫል ላይ በቀረበበት አጋጣሚ ለዶቼቨሌ የተናገረችው ነው፡፡ ኒዤሪያዊት የፊልም ባለሞያ ፊልሟ ውስጥ አማርኛ ጽሑፍ በማስገባት ለአማርኛ ቋንቋ መቆርቋሯን አሳይታለች ኒዤሪያዊቷ የፊልም ባለሞያ ራማቱ ኪየታ፤ አማርኛ የአፍሪካ ኅብረት ይፋዊ ቋንቋ እስኪሆን ጥረቴን አላቋርጥም ትላለች። ኒዤሪያዊቷ የፊልም ዳይሬክተር በዓለም ዙሪያ በሚገኙ የፊልም ፌስቲቫሎች ላይ በመሳተፍ ለአማርኛ ቋንቋ መሟገቷን ቀጥላለች። ፊልሟ ሆላንድ ከተማ ሪያልቶ ሲኒማ ቤት ውስጥ ለእይታ ከቀረቡ ሌሎች ፊልሞች ለየት ስለሚያደርገው ነገር ስትናገርም፣ «ትግሌ ውብ ባህላችን ተጠብቆ ለትውልድ እንዲሸጋገር ማድረግ ነው፤ ባህላችንን ካልተንከባከብን እየደበዘዘ ለመክሰም ጊዜ አይፈጅበትም» ብላለች፡፡ በተጓዘችበት ሥፍራ ሁሉ አማርኛ ከአፍሪካ ኅብረት ይፋዊ መግባቢያዎች አንዱ እንዲሆን መወትወቷን እንደማታቋርጥም ሳትናገር አላለፈችም። ከታዋቂ ሰዎች እስከ ሀገር መሪዎች ድረስ ባገኘችው አጋጣሚ ውትወታዋን አለመተዋን፣ በአንድ አጋጣሚም የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን አዲስ አበባ ውስጥ በዚሁ ጉዳይ አነጋግራ እንደነበር ገልጻለች።