የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) በአሠሪና ሠራተኛ ረቂቅ አዋጅ ላይ ባለው አቋም ላይ መንግሥት የማያወያየው ከሆነ እስከ ሥራ ማቆም የደረሰ ዕርምጃ እንደሚወሰድ ካሳወቀ በኋላ፣ መንግሥት ከኢሠማኮ አመራሮች ጋር ለመነጋገር የውይይት መድረክ እንዲዘጋጅ መግባባት ላይ መደረሱ ተገለጸ፡፡
አዲሱ ረቂቅ አዋጅ የሠራተኞችን መብት የሚነካና የኢንዱስትሪ ሰላምን የሚያናጋ በመሆኑ መፅደቅ እንደሌለበት፣ ባለፈው ሳምንት የተካሄደው ኢሠማኮ ጠቅላይ ምክር ቤት የአቋም መግለጫ አውጥቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የኢሠማኮ ጠቅላይ ምክር ቤት ረቂቅ አዋጁን በተመለከተ የደረሰበትን ድምዳሜ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝና ለሌሎች የመንግሥት ባለሥልጣናት በድጋሚ በማሳወቁ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ከኢሠማኮ ጋር ለመነጋገር ሐሙስ ጥቅምት 23 ቀን 2010 ዓ.ም. መግባባት ላይ መደረሱን ሪፖርተር ያገኘው መረጃ ያስረዳል፡፡
የውይይት መድረኩ በሚቀጥለው ሳምንት በአንዱ ቀን እንዲካሄድ በቃል የተገለጸላቸው መሆኑን ሪፖርተር ያነጋገራቸው የኢሠማኮ የሥራ ኃላፊዎች ገልጸው፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎን በስልክ ማነጋገራቸውን አረጋግጠዋል፡፡
ከኢሠማኮ የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት በኢሠማኮ ጥያቄ መሠረት በረቂቁ ላይ ለመምከር በሚቀጥለው ሳምንት ፕሮግራም እንዲያዝ ስምምነት ተደርሷል፡፡ ይህንንም የምክክር መድረክ የሚያመቻች ባለሥልጣን መሰየሙ ታውቋል፡፡
በመንግሥትና በኢሠማኮ መካከል በሚደረገው የውይይት መድረክ በረቂቁ ላይ ሲመክሩ የነበሩት የአሠሪዎች ፌዴሬሽንና የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካዮች፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ተወካይ በሚገኙበት እንደሚካሄድ ይጠበቃል፡፡
ባለፈው ሳምንት በተካሄደው የኢሠማኮ ጠቅላይ ምክር ቤት ጉባዔ መንግሥት የማያነጋግራቸው ከሆነ መጀመሪያ በሰላማዊ ሠልፍ፣ በዚህ ካልተሳካም በሥራ ማቆም አድማ መብታችንን እናስከብራለን በሚል የአቋም መግለጫ ማውጣቱ ይታወሳል፡፡ አሁን ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት የተገኘው ይሁንታ በረቂቁ ላይ ለመደራደር የሚያስችላቸውን አጋጣሚ የፈጠረ በመሆኑ፣ መንግሥት በወሰደው ዕርምጃ ኢሠማኮ መደሰቱ ተገልጿል፡፡
ሆኖም ውይይቱ ኢሠማኮ በሚፈልገው ደረጃ የአዋጁ ረቂቅ ለማስተካከል ያስችላል አያስችልም የሚለው ጉዳይ፣ ከውይይቱ በኋላ የሚታይ ይሆናል ተብሏል፡፡