በብቸኝነት አህጉራዊውም ሆነ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን በማስተናገድ ከሚታወቀው የአዲስ አበባ ስታዲየም በተጨማሪ፣ በመጠናቀቅ ላይ ያለው አዲሱ የባህር ዳር ስታዲየም በዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) ዕውቅና ማግኘት ይችል ዘንድ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለፊፋ ጥያቄ ሊያቀርብ መሆኑ ተሰማ፡፡ አዲሱ የባህር ዳር ስታዲየም ዕውቅና ከተሰጠው በውድድር ዓመቱ ኢትዮጵያን በመወከል በአፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮናና ለአፍሪካ ክለቦች ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ የሚሳተፉት ቅዱስ ጊዮርጊስና ደደቢት እግር ኳስ ክለቦች በሜዳቸው የሚያደርጉት ጨዋታ ይስተናገድበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ የፌዴሬሽን ምንጮ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ የዓለም አቀፍ ደረጃን ጠብቆ እንደተገነባ የሚነገርለት ሁለገቡ የባህር ዳር ስታዲየም፣ አራተኛውን የመላ ኢትዮጵያ ጨዋታዎችን በአጥጋቢ ሁኔታ ከማስተናገዱ ሌላ ከብሔራዊ ሊግ ወደ ፕሪሚየር ሊግ የሚያድጉ ሁለት ክለቦችን ለመለየት፣ በ16 የብሔራዊ ሊግ ክለቦች መካከል የተደረገው ጨዋታም መካሄዱ ይታወሳል፡፡