የጀርመን የትምህርትና የባህል ማዕከል በሆነችው ላይፕዚሽ ከተማ ከንቲባ የሚመራ የልዑካን ቡድን አዲስ አበባ ገባ፡፡ የልዑካን ቡድኑ የካቲት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ እየተካሄደ ያለውን የኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታና የቀላል ባቡር ፕሮጀክቶችን ጎብኝቷል፡፡
የልዑካን ቡድኑ ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ጋር የካ አባዶ እየተገነቡ ያሉትን የኮንዶሚኒየም ቤቶች ተመልክቷል፡፡
የከንቲባ ድሪባ ረዳት አቶ ወርቁ አባተ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የላፕዚሽ ከተማ የአዲስ አበባ ከተማ እህት በመሆንዋ በብዙ መስኮች የቴክኒክ ድጋፎችን ስትሰጥ ቆይታለች፡፡
በተለይ ስድስት ኪሎ ከሚገኘው አንበሳ ግቢ አንበሶችን ወደ ፒኮክ መናፈሻ ለማዘዋወር ለተቋቋመው ፕሮጀክት፣ የላይፕዚሽ ከተማ ዋነኛ ተሳታፊ ናት፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ለስድስት ኪሎ አንበሶች በየዓመቱ የሕክምና አገልግሎት ትሰጣለች፡፡
ላይፕዚሽ ከተማ በዱር እንስሳት ማቆያ የምትታወቅና ብዙ ልምድ ያላት በመሆኑ፣ የፒኮክ መናፈሻ ለአንበሶች መኖሪያ እንዲሆን ሲታሰብ ዋነኛ ተዋናይ በመሆን ፕላኑን ሠርታለች፡፡
ይህንን የቴክኒክ ድጋፍ ከፍ በማድረግ ላይፕዚሽ ከተማ በቤቶችና በከተማ ባቡር ዘርፍ ያላትን ተሞክሮ ለአዲስ አበባ እንድታካፍል የተለያዩ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑ ታውቋል፡፡
የልዑካን ቡድኑ በአራት ቀን ቆይታው ሁለቱ ከተሞች እህትማማች የሆኑበትን አሥረኛ ዓመት በዓል ከአዲስ አበባ አቻው ጋር እንደሚያከብር ታውቋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሁለቱ ከተሞች ንግድ ምክር ቤቶች የቢዝነስ ፎረም ይካሄዳል፡፡ አቶ ወርቁ እንደገለጹት፣ የሁለቱ ከተሞች ግንኙነታቸውን ለማጠናከር የቢዝነስ ፎረሙ ትልቅ ድርሻ ይኖረዋል፡፡
ከወራት በፊት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ድሪባ የሚመራ የልዑካን ቡድን ወደ ላይፕዚሽ ከተማ ተጉዞ ነበር፡፡ በወቅቱ የሁለቱን ከተሞች አሥረኛ ዓመት በዓል ከመከበሩም በላይ፣ የተለያዩ የኢንቨስትመንትና የንግድ ፎረሞች ተካሂደዋል፡፡