የአፍሪካ እግር ኳስን ወደ ተሻለ የዕድገት ደረጃ ለማድረስ የዓለም አቀፍ እግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) እና የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) በቁርኝት ለመሥራት ተስማሙ፡፡
በኢኳቶሪያል ጊኒ የተካሄደውና በአይቮሪኮስት አሸናፊነት በተጠናቀቀው የአፍሪካ ዋንጫ አጋጣሚ ፊፋ እና ካፍ ስምምነት ላይ የደረሱት በቴክኖሎጂና ትምህርት፣ የተጫዋቾች ልምምድ፣ በዳኝነት ሕጋዊ ፈቃድና ዕድገት፣ በተጫዋቾች ሕጋዊ የአመዘጋገብ ዋስትና አመራርና በስፖርት የሕክምና ዕድገትን እንቅስቃሴን ላይ መሆኑን ካፍ በድረ ገጹ አስፍሮታል፡፡
የሁለቱ ተቋማት ስምምነት ተከትሎ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ አዘጋጅዋ ኢኳቶሪያል ጊኒና ጋና ባደረጉት ጨዋታ ስለተፈጠረው ውዝግብ የፊፋ ፕሬዚዳንት ሴፕ ብላተር ተጠይቀው፣ ‹‹በአጠቃላይ ኃላፊነቱን መውሰድ ያለበት ካፍ ነው፤›› ብለዋል፡፡ የካፍ ፕሬዚዳንት ኢሳ ሐያቱ በበኩላቸው፣ ‹‹የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ ውሳኔ የተሰጠው በደንቡ መሠረት ነው፤›› በማለት መልስ ሰጥተዋል፡፡
የ30ኛ አፍሪካ ዋንጫን ከ23 ዓመት በኋላ ያነሳችው የምዕራብ አፍሪካዋ አይቮሪኮስት ተጋጣሚዋን ጋናን በ9 ለ8 መለያ ምት በማሸነፍ ነው፡፡ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችው ጋና ከ33 ዓመት በፊት ከ13ኛው አፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅዋ ሊቢያ ጋር ተገናኝታ በተመሳሳይ ሁኔታ በመለያ ምት ማሸነፏ ይታወሳል፡፡
በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ስድስት ጊዜ በማሸነፍ ግብፅ ስትመራ፣ ጋናና ካሜሮን በተመሳሳይ ሁኔታ አራት አራት ጊዜ አሸናፊ ሆነዋል፡፡ ናይጄሪያ ደግሞ ሦስት ጊዜ በማሸነፍ ትከትላለች፡፡