ሰሞኑን ሁለት ተሽከርካሪዎች በመስመሩ ላይ ጉዳት አድርሰዋል
በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ በሚገኘው የቀላል ባቡር ፕሮጀክት ላይ እየደረሰ ያለውን አደጋ ለመከላከል የሚያስችል ረቂቅ ሕግ መዘጋጀቱ ተጠቆመ፡፡
የቀላል የባቡር ፕሮጀክቱ የመጨረሻ ምዕራፍ የሙከራ አገልግሎት የተጀመረ ቢሆንም፣ ሰሞኑን በመስመሩ ላይ የተከሰቱ ሁለት አደጋዎች ፕሮጀክቱን በማከናወን ላይ ያሉትን ቻይናውያን ሳይቀር ሥጋት ላይ ጥለዋል፡፡
በመሆኑም የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ተሽከርካሪዎችና እግረኞች በምን ሁኔታ እንደሚስተናገዱ፣ በተለይ ተሽከርካሪዎች ለሚያደርሱት ጉዳት ተጠያቂ የሚያደርግ ረቂቅ ሕግ መረቀቁንና ለውይይት ለሕዝብ ሊቀርብ መሆኑን፣ የጽሕፈት ቤቱ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደረጀ ተፈራ አስረድተዋል፡፡
የካቲት 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ሌሊቱን አንድ የግል ንብረት የሆነ ከባድ የጭነት ተሽከርካሪ ከነጭነቱ ሳሪስ ኦይል ሊቢያ ዲፖ ፊት ለፊት ያለውን የባቡር ሐዲድ አጥር ጥሶ ገብቷል፡፡ ተሽከርካሪው ምንም እንኳን በሰው ሕይወት ላይ አደጋ ባያስከትልም፣ እስካሁን በውል ያልታወቀ ኪሳራ ማድረሱ ታውቋል፡፡ አደጋ የደረሰበት የመስመሩ አጥር መልሶ ከተገጣጠመ በኋላ፣ ባቡር እንዲያልፍበት ተደርጎ ጥንካሬው ሲፈተሽ ችግር እንደሌለው መረጋገጡን አቶ ደረጀ ገልጸዋል፡፡ ወጪውን በሚመለከት የኢንሹራንስ ግምት እየተጠበቀ መሆኑንም አክለዋል፡፡
በተለይ ከመንጃ ፈቃድ አሰጣጥ ጋር በተገናኘ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ተገቢ መሆኑን አስተያየት ሰጪዎች ተናግረው፣ ወደፊት ባቡሩ ሙሉ በሙሉ ሥራ በሚጀምርበት ወቅት ምን ያህል የከፋ ነገር ሊገጥም እንደሚችል ጠቋሚ በመሆኑ ሕግ መውጣቱ ተገቢ መሆኑን፣ በፍጥነት ፀድቆ ወደ ተግባር መሄድ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡