Friday, June 9, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየአዲስ አበባ አስተዳደር በመሬት አቅርቦት ኢ-ፍትሐዊነት ተወቀሰ

የአዲስ አበባ አስተዳደር በመሬት አቅርቦት ኢ-ፍትሐዊነት ተወቀሰ

ቀን:

በሁለት ክፍላተ ከተሞች ብቻ 238 ቦታዎች ለጨረታ ቀረቡ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት አቀራረብ የከተማውን ሰሜናዊ ክፍል የረሳና የነዋሪዎችን ፍላጎት ያላገናዘበ ነው በሚል ተወቀሰ፡፡

ወቀሳው የቀረበው ሰሞኑን እየተካሄደ በሚገኘው የአዲስ አበባ አስተዳደር የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ላይ ነው፡፡ ይህ ወቀሳ ሊቀርብ የቻለው ለጨረታ የሚቀርቡት አብዛኛዎቹ ቦታዎች፣ በተለይም ለመኖሪያ ቤት የሚቀርቡት ሰሜናዊ ክፍሉን የረሱ ናቸው በማለት ነው፡፡

አብዛኛዎቹ ጨረታዎች በቦሌ ክፍለ ከተማ ሲኤምሲ፣ በአያት፣ በቡልቡላ፣ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ፣ አዲሱ የፍጥነት መንገድ ባለበት በቱሉ ዲምቱ አካባቢ ላይ ትኩረት ያደረጉ መሆናቸው ተተችቷል፡፡ በተለይ በሰሜን ማዘጋጃ፣ በፈረንሳይ ሌጋሲዮንና ቤላን የመሳሰሉ አካባቢዎችን የረሱ ከመሆናቸውም በላይ፣ የከተማው የመሠረት ልማት ዕድገት ወደ ምሥራቃዊው የከተማው ክፍል ብቻ እንዲሆን አድርጓል ተብሏል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ለጨረታ የሚቀርቡት ቦታዎች ስፋታቸው የተለያዩ አለመሆኑ እንደ ድክመት ተነስቶ፣ የከተማው መሬት ልማትና ማናጅመንት ቢሮ ተወቅሶበታል፡፡ ለአብነትም መካከለኛ ገቢ ያለው የኅብረተሰብ ክፍል እንዳቅሙ 105 ካሬ ሜትር ስፋት ያለው ቦታ፣ የተሻለ አቅም ያለው የኅብረተሰብ ክፍል ደግሞ ለመኖሪያ ቤት ከአንድ ሺሕ ካሬ ሜትር ያላነሰ ቦታ ሊፈልግ እንደሚችል ተጠቅሷል፡፡

ነገር ግን ለጨረታ የሚቀርቡት ቦታዎች እነዚህን ቁም ነገሮች ከግንዛቤ የከተቱ አይደሉም በሚል መሬት ቢሮው ወቀሳ ቀርቦበታል፡፡

ከሊዝ ጨረታ በተጨማሪ የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ የኢንዱስትሪ ቦታ አቅርቦትና በመልሶ ማልማት ቦታዎች ላይ ዝቅተኛ የሥራ አፈጻጸም አስመዝግቧል በሚል ተገምግሟል፡፡ መሬት ቢሮው በጥሩ ጎን የታየለት ጉዳይ በየወሩ ሳይቋረጥ መሬት ለጨረታ ማቅረቡ ሲሆን፣ ይኼም ቢሆን ለጨረታ የሚቀርቡት ቦታዎች ቁጥር ዝቅተኛ በመሆኑ የመሬት ሊዝ ዋጋ የተረጋጋ እንዳይሆን አድርጓል በሚል መገምገሙን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የከተማው መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ኃይሌ በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡ የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ እየተተቸ ባለበት ወቅት በአቃቂ ቃሊቲና በቦሌ ክፍላተ ከተሞች 238 ቦታዎችን ለጨረታ አቅርቧል፡፡

ባለፈው ዓርብ ይፋ በተደረገው ጨረታ በቦሌ ክፍለ ከተማ ሲኤምሲ፣ አያትና ቡልቡላ አካባቢዎች ለመኖርያ ቤት፣ ለቢዝነስ፣ ለቅይጥና ለአፓርትመንት የሚውሉ 116 ቦታዎችን ለጨረታ አቅርቧል፡፡

በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማም እንዲሁ ቱሉ ዲምቱ አካባቢ ለመኖሪያ አገልግሎት ብቻ የሚውሉ 122 ቦታዎችን ለጨረታ አቅርቧል፡፡ ከሌሎች ጊዜያት ጋር ሲነፃፀር ለጨረታ የቀረቡት ቦታዎች ብዛት ያላቸው መሆኑ ታውቋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ