‹‹ኣዘባ›› የተሰኘና በኣዘባ አካባቢ ተወላጆች የትግል ሕይወት ላይ ያተኮረ ፊልም የሕወሓትን 40ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ምክንያት በማድረግ ተመርቋል፡፡ አምባሳደር ሥዩም መስፍን የካቲት 6 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ ባህል አዳራሽ በይፋ የመረቁት ‹‹ኣዘባ›› ፊልም መነሻው ‹‹ፅንኣት›› የተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡
የፊልሙና ምርቃቱ አስተባባሪ አቶ ተወልደ ግደይ ዘጋቢ ፊልሙ በዋነኛነት ከ1966 እስከ 1983 ዓ.ም. በኣዘባ የነበረውን ትግል ያሳያል ብለዋል፡፡ ፊልሙ በፎቶግራፍና ቪዲዮ መረጃዎች የተደገፈና በትግሉ የነበሩ ሚሊሺያዎችን አስተያየትም ያካተተ ነው፡፡ ፊልሙ በተለይም አብርሃ የተባለ ታጋይ እጁን ላለመስጠት በመሣሪያው በቀረው አንድ ጥይት ጠላቱን ገድሎ 300 ሜትር ጥልቀት ባለው ገደል ገብቶ ራሱን የሰዋበትን ታሪክ ያጎላል ብለዋል፡፡ ፊልሙ ልጆቹና ቤተሰቡን ለሰዋ የአካባቢው ተወላጅ የበለጠ ትርጉም ይሰጣልም ብለዋል፡፡
የ‹‹ፅንኣት›› ጸሐፊ ጋዜጠኛ ኃይለ ሀድጉ እንደሚለው፣ ታሪኩ በፊልም መዘጋጀቱ ተደራሽነቱን ያሰፋዋል፡፡ ታሪኩን በቀላሉ ለትውልድ ለማስተላለፍም ያግዛል፡፡ ፊልሙ በአካባቢው የተሠራውን ታሪክ ለተቀረው የአገሪቱ ሕዝብ የሚያስተዋውቅ ነው ብሏል፡፡
ሁለት ሰዓት የሚፈጀው ፊልሙ የተዘጋጀው በበርኸ ኃይሌ ሲሆን፣ በ200 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በቀጣይ በኣዘባ፣ በዓዲግራት፣ በመቐለና ሌሎችም አካባቢዎች ይታያል፡፡