የዘንድሮው የዘ ናይል ፕሮጀክት የሙዚቃ ድግስ መዳረሻውን አሜሪካ አድርጓል፡፡ 13 ሙዚቀኞች የተካተቱበት ቡድኑ በአሜሪካ የተለያዩ ከተሞች ኮንሰርት ያቀረበ ሲሆን፣ ሲምፓዝየሞችም ተካሂደዋል፡፡
የናይል ፕሮጀክት ድረ ገጽ እንደሚያሳየው፣ አባላቱ ከሙዚቃ ኮንሰርቶች በተጨማሪ በስታንፎርድና ቤርክሊ ‹‹ዘ ናይል ኤንድ አፍሪካን አይደንቲቲ፤››፣ ‹‹ሚውዚክ ኮላቦሬሽን ኤንድ ዋተር ኮኦፕሬሽን›› እና ‹‹ፉድ አሎንግ ዘ ናይል›› በሚሉ ርእሶች ወርክሾፖች ተካሂደዋል፡፡ በወርክሾፑ በናይል ተፋሰስ አገሮች መካከል የነበረውና ያለው ውዝግብ ተነስቷል፡፡ መድረክ ላይ የሚያቀርቧቸው ሙዚቃዎች ከዳሰሷቸው ርዕሰ ጉዳዮች በተጨማሪ ስለቅኝ ግዛትና ፆታዊ ጉዳዮች ውይይት ተደርጓል፡፡
ዘ ናይል ፕሮጀክት ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአሥር የዓባይ ተፋሰስ አገሮች በተውጣጡ ሙዚቀኞች የተዋቀረ ነው፡፡ መሥራቾቹ ግብፃዊው ኢትኖሚውዚኮሎጂስት ሚና ጊርጊስና ኢትዮጵያዊቷ መክሊት ሐደሮ ናቸው፡፡ በፕሮጀክቱም ዓባይ ወንዝ ያስተሳሰራቸው የሱዳን፣ የደቡብ ሱዳን፣ የኤርትራ፣ የኬንያ፣ የታንዛኒያ፣ የኡጋንዳ፣ የታንዛኒያ፣ የሩዋንዳ፣ የብሩንዲና የኮንጎ ሙዚቀኞችን አሰባስበዋል፡፡
ከመሥራቾቹ አንዱ ሚና እንደሚለው፣ ውይይቱ ያስፈለገው ከዓባይ ተፋሰስ አገሮች ውዝግብ ጀርባ ያለው እውነታ እንዲታወቅ ነው፡፡ ‹‹ከፅንሰ ሐሳብ ባለፈ አሁን የሚታየውን ሁነት መነሻ ሁሉም እንዲገነዘብ እንፈልጋለን፤ ከዓባይ ጋር ተያይዘው በሚመጡ ውዝግቦች የእኛ የናይል ተፋሰስ አገሮች ተወላጆች ሚና ምንድን ነው? የሚለውም መታወቅ አለበት፤›› ብሏል፡፡
ሚና አፍሪካዊ ማንነት ላይ የሚነሱ ጥያቄዎችን አንስቷል፡፡ እንደ ምሳሌ ግብፃውያን እንደ ዓረቦች እንደሚቆጠሩ ጠቅሶ፣ መሰል የማንነት ጥያቄዎች የዓባይን ጉዳይ ያወሳስቡታል ብሏል፡፡ እንደእሱ ገለጻ፣ ሙዚቀኞቹ ወደ መድረክ ሲወጡ የማንነትና የውኃ ጥያቄ ጋብ ይላል፡፡ ‹‹ሙዚቃ ሁሉንም እንዲናገር እናደርጋለን፤›› ሲል የመድረኩን ስሜት ይገልጸዋል፡፡ የዓባይ ተፋሰስ አገሮች ሙዚቀኞችን በአንድ መድረክ መመልከት ለብዙዎች እንደሚያስደስት ሳይጠቅስም አላለፈም፡፡
የሊንከን ሴንተር እንዳስታወቀው፣ ልዩ ጥምረት የሚታይበት ናይል ፕሮጀክት ሙዚቀኞች በናይል ተፋሰስ አገሮች መካከል ያለውን ትስስር የሚያሳዩ ሙዚቃዎች አስደምጠዋል፤ ተጣምረው ምሥራቅ አፍሪካዊ ድባብ ፈጥረዋል፡፡ የተሳተፉት ኢትዮጵያውያን መክሊት ሐደሮ፣ እንድሪስ ሐሰን፣ ዳዊት ሥዩም፣ ሰላምነሽ ዘመነ፣ ዮርጋ መስፍን፣ መኳንንት መለሰና አሥራት አያሌው ናቸው፡፡
ናይል ፕሮጀክት እ.ኤ.አ. በ2013 ‹‹አስዋን›› የተሰኘ አልበም አሳትሟል፡፡ ሱዳናዊው የማሳንኮፕ (የሱዳን ባህላዊ ሙዚቃ መሣሪያ) ተጫዋች አሕመድ ሰይድ አቡአማን እና ግብፃዊው ቫዮሊን ተጨዋች አልፍሬድ ጋሚል ጥምረት የታየበት ‹‹ጎንግዋብ›› የተሰኘ ዘፈንም ተወዳጅ ነው፡፡
እነዚሁ ከተለያዩ አገሮች የተውጣጡት የናይል ሙዚቃ ፕሮጀክት አባላት ቀጣይ ሥራቸውን የፊታችን መጋቢት 10 እና 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊንከን ሴንተርና ፔስ ዩኒቨርሲቲ እንደሚያቀርቡ ታውቋል፡፡