12ኛውን የአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዝግጅት ኢትዮጵያ እንድታዘጋጅ የአፍሪካ አትሌቲክስ ኮንፌዴሬሽን (ሲኤኤ) ባገኘችው ፈቃድ መሠረት ከየካቲት 26 እስከ 29፣ 2007 ዓ.ም. የሚካሄደው ዝግጅት እየተጠናቀቀ መሆኑን የስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ አብዲሳ ያደታ አስታወቁ፡፡
ዝግጅቱ ከአደረጃጀቱ፣ ከአሠራር፣ ከሀብት ምደባ፣ ከዕቅድ ዝግጅትና ፋሲሊቲ ዝግጅት ጋር በተያያዘ ሰፋፊ ሥራዎች እንደተሠሩ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘም ከየካቲት 22 እስከ 24 በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ ጉባኤ ይከናወናል ብለዋል፡፡ በውድድር ወቅት ለሚያስፈልጉ የወንበር፣ የቴክኖሎጂ አገልግሎቶች የአዳራሽ አገልግሎት፣ የትርጉም አሰጣጥና የሆቴል ቤቶች ሥራ መጠናቀቁንም አክለዋል፡፡
ለአራት ቀናት በሚካሄደው በዚህ ውድድር 47 አገሮች እንደሚሳተፉ የተገለጸ ሲሆን፣ ከነዚህ ውስጥ እስከ ቅርብ ጊዜ 34 የሚሆኑ አገሮች የተሳታፊዎቻቸውን ዝርዝር መረጃ ልከዋል፡፡ ሁሉም ተወዳዳሪ አገሮች በቀላሉ ቪዛ እንዲያገኙ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በመተባበር እንቅስቃሴ እየተደረገ እንዳለም ተገልጿል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ ከሴራሊዮን ለሚመጡ ተካፋይ አገሮች በተለይ ከኢቦላና ፀረ ዶፒንግ ችግሮችን ለመፍታት ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ባለሙያዎች እንደተዘጋጁ ተናግረዋል፡፡
የስፖርት ሜዳን ከማዘጋጀት ጋር በተገናኘ ከአዲስ አበባ ስታዲየምና በዙሪያው የሚገኙ የቅርጫት ኳስ፣ ቮሊቮል፣ የአትሌቶች ማሟሟቂያ ሜዳ፣ የፅዳት ሥራና የማስወዋብ ሥራ ለዕይታ በሚያመች ሁኔታ ተዘጋጅቶ ሥራው ተጠናቋል ብለዋል፡፡