ኢትዮጵያ ስድስቱን የዓለም ጤና ጉባዔን ግቦች ለማሳካት ብዙ ጊዜ እንደሚያስፈልጋት፣ አንድ የዓለም አቀፍ ምግብ ፖሊሲ ጥናት ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪ ጠቆሙ፡፡
የካቲት 18 ቀን 2007 ዓ.ም. በኢሊሊ ሆቴል በተካሄደው የሙሉ ቀን ጉባዔና እ.ኤ.አ. የ2014 የዓለም የሥነ ምግብ ሪፖርት ይፋ በሆነበት መድረክ፣ ኢትዮጵያ ግቦቹን ለማሳካት በፊት ከነበረችበት ዜሮ ስኬት አንዱን በማሳካት እንደሰመረላትና የሚቀሩትን ግቦች ለመምታት ጊዜ እንደሚወስድባት የጠቆሙት፣ የዓለም አቀፍ የምግብ ፖሊሲ ጥናት ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪ የሆኑት ሚስተር ላውረንስ ሐዳድ ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ በኩል የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዴኤታን ወክለው የተገኙት አማካሪው አቶ ታዬ ቶሌራ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ የምዕተ ዓመቱን የልማት ግቦችን በማሳካቱ ረገድ ተጠቃሽ ከነበሩት የአፍሪካ አገሮች አንዷ መሆኗንና በተለይም በሕፃናት ሞት ቅነሳ ረገድ ያስመዘገበችው ስኬት የላቀ መሆኑን ተከትሎ፣ በቅርብ ዓመታት የዓለም ጤና ጉባዔን ግቦች ለማሳካት ዕድሉ እንዳላት ጠቁመዋል፡፡
ከስድስቱ የዓለም ጤና ጉባዔ ግቦች መካከል አንደኛውን ማለትም የሕፃናትን መቀጨጭ 40 በመቶ ካሳኩት 64 አገሮች ጎራ የተመደበችው ኢትዮጵያ፣ ስምንት የአፍሪካ አገሮች ብቻ የተወከሉበትን ሁለት ግቦችን ያሳኩ አገሮች ተርታ ለመቀላቀል የሚሳካላት ቢመስልም፣ ሁሉንም ግቦች በማሳካቱ ረገድ ግን ረዘም ያለ ጊዜ ሊወስድባት እንደሚችል በባለሙያዎች ተጠቁሟል፡፡
ስድስቱ የዓለም ጤና ጉባዔ ግቦች የሕፃናት መቀጨጭን በ40 በመቶ መቀነስ፣ ለአቅም ሔዋን በደረሱ ሴቶች ላይ የሚታየውን የደም ማነስን በ50 በመቶ መቀነስ፣ በዝቅተኛ የውልደት ክብደት የሚወለዱ ሕፃናትን ቁጥር በ30 በመቶ መቀነስ፣ ከመጠን በላይ የሰውነት ክብደት ይዘው የሚወለዱ ሕፃናትን መከላከል፣ የእናት ጡት ምግብን በ50 በመቶ ማሳደግና የሕፃናትንና የልጆችን ብክነት መግታት ናቸው፡፡