የ14 ዓመቷ ትውልደ ኢትዮጵያዊት ታዳጊ ብሪቱ አህመድ ትባላለች፡፡ ትውልዷም ዕድገቷም በአውስትራሊያ ነው፡፡ ስለአገሯ ኢትዮጵያ ብዙ የምታውቀው የላትም፡፡ መላው ቤተሰቧ ኑሮውን ያደረገው እዚያው አውስትራሊያ ነው፡፡ ሜልቦርን በሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት በመማር ላይ ትገኛለች፡፡
የመማር ዕድል ያላገኙት ወላጅ እናቷና ከዘጠነኛ ክፍል ሊዘልሉ ያልቻሉት የአባቷ የትምህርት ሁኔታ ያስጨንቃት ነበር፡፡ ያልተማሩበት ምክንያትም ሳታውቅ ብዙ ቆይታ ነበር፡፡
ብሪቱ በምትማርበት ትምህርት ቤት ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ክለቦች ውስጥ ትሳተፋለች፡፡ በሴቶች ጉዳይ ላይ በሚሠራው ክለብ ውስጥም ፕሬዚዳንት ናት፡፡ ከአራተኛ ክፍል ጀምሮ በበርካታ ክለቦች በመሳተፍ የአቅሟን አበርክታለች፡፡ ነገር ግን በአገሯ ኢትዮጵያ ስላሉ አንዳንድ ችግሮች ታናሽ ወንድሟ ኢትዮጵያን ጐብኝቶ እስኪነግራት ድረስ በአገር ውስጥ በበጎ ፈቃደኛ ሥራዎች ላይ የመሰማራት ህልም አልነበራትም፡፡
‹‹ታናሽ ወንድሜ ከሁለት ዓመት በፊት ኢትዮጵያ መጥቶ ነበር፡፡ ያረፈውም የወላጆቻችን የትውልድ ቀዬ በሆነው ጋራ ሙለታ አካባቢ ነበር፡፡ ስለአካባቢው ብዙ ነገሮች ቢነግረኝም የትምህርት ቤት እጥረት በመኖሩ ብዙ ሰዎች የትምህርት ዕድል እንደማያገኙ ሲነግረኝ በጣም ደነገጥኩ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮም ስለችግሩ በስፋት ማሰብ ጀመርኩ፤›› ትላለች፡፡
በ2014 አጋማሽ ላይ ግን ለችግሩ መቀረፍ የበኩሏን ማበርከት የምትችልበት አጋጣሚ ተፈጠረ፡፡ ይኸውም ተማሪዎች እንደ ለውጥ ሐዋርያ ሆነው በመጡበት ማኅበረሰብ በጎ አሻራ ማሳረፍ ስለመቻላቸው የሚፈትሽ ፕሮጀክት እንዲነድፉ ተደረገ፡፡ በፕሮጀክቱ የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ ለፕሮጀክቱ ማስኬጃ የሚሆን የገንዘብ ድጋፍ የሚያገኙበት ነበር፡፡ በውድድሩም የመጡበትን ማኅበረሰብ ችግር ማወቅ፣ ችግሩን የሚቀረፍበትን የመፍትሔ ሐሳብ ማቅረብ ትልቁን ድርሻ ይይዛል፡፡ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ባለው በዚህ ውድድር ላይ ብሪቱም ተሳታፊ ነበረች፡፡
ከቀረቡት በርካታ ፕሮጀክቶች መካከልም አንደኛ ሆኖ የተመረጠው የብሪቱ ፕሮጀክት ነበር፡ ‹‹ፕሮጀክቴን የቀረፅኩት ወንድሜ ስለነገረኝ ጋራ ሙለታ አካባቢ ስላለው ውስን የትምህርት ዕድል ሲሆን፣ ትምህርት ቤት መክፈትን የተመለከተ ነው፤›› የምትለው ታዳጊዋ፣ ከቀረቡት ፕሮጀክቶች አንደኛ ሆኖ በመመረጡ 20 ሚሊዮን የአውስትራሊያ ዶላር ከአውስትራሊያ መንግሥት እንደተሸለመች ትናገራለች፡፡ ሽልማቱንም ለፕሮጀክቱ ማስኬጃ እንደምታውለው ቃል ገብታለች፡፡
ይህንን የገለጸችው በምሥራቅ ሐረርጌ ጋራ ሙለታ አካባቢ ለመክፈት ስላሰበችው ትምህርት ቤት ባለፈው ዓርብ (የካቲት 20) በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሰጠችው ጋዜጣዊ መግለጫ ነው፡፡ ለመገንባት ያቀደችው ትምህርት ቤት ከመዋለ ሕፃናት እስከ 12ኛ ክፍል ትምህርት የሚሰጥ ሲሆን፣ ግንባታው በዚህ ዓመት እንደሚጀመርና በቀጣይ ሦስት ዓመታት ውስጥ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ለሪፖርተር ገልጻለች፡፡ ለፕሮጀክቱ መሳካትም መንግሥት አስፈላጊውን ትብብር እንደሚያደርግ የገለጹት ቃል አቀባዩ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ‹‹በክልሉ በኩል የሚያስፈልጉ ትብብሮችን እንድታገኝ በጋራ እንሠራለን፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡