– የሁለተኛ ምክትል ዋና ኦዲተር ሹመትም ፀድቋል
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመጀመርያ የሹመት ዘመናቸውን ያገባደዱትን የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ዋና ኦዲተርን ሁለተኛ የሥራ ዘመን ሹመት አፀደቀ፡፡
በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በድጋሚ የታጩት አቶ ገመቹ ዱቢሶ፣ ላለፉት ስድስት ዓመታት በዋና ኦዲተርነት መሥሪያ ቤቱን ሲመሩ ቆይተዋል፡፡ በተጨማሪም ከፓርላማው የመንግሥት ወጪ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ጋር በጋራ በመሆን፣ በተለይ ባለፉት ሦስት ዓመታት ውጤታማ ተግባር እንዳከናወኑ ፓርላማው ባለፉት ዓመታት መስክሮላቸዋል፡፡ ኦዲት የሚደረጉ የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶችን ኦዲት የማድረግ አቅም ከሞላ ጎደል መቶ በመቶ ከማድረሳቸውም በተጨማሪ፣ ኦዲት የተደረጉ መሥሪያ ቤቶች ስህተታቸውን እንዲያስተካክሉ ከፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ ጋር እያከናወኑ ላለው ተግባር ከፍተኛ አድናቆት ከፓርላማው በተደጋጋሚ ተሰጥቷቸዋል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር ማቋቋሚያ አዋጅ ለአንድ ዋና ኦዲተር ሁለት የሥራ ዘመኖችን የሚፈቅድ ሲሆን፣ እያንዳንዳቸው ስድስት ዓመታትን ይወክላሉ፡፡ አቶ ገመቹ ዱቢሶ የመጀመርያውን ጨርሰው መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. በድጋሚ ለተጨማሪ ስድስት ዓመታት ተሹመዋል፡፡
አቶ ገመቹ እ.ኤ.አ. በ1987 ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በአካውንቲግ የተመረቁ ሲሆን፣ እ.ኤ.አ. በ1996 ከግላስኮ ካሌደኒያን ዩኒቨርሲቲ የማስተርስ ዲግሪያቸውን በፋይናንስ አስተዳደር መያዛቸውን የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል፡፡
በዚሁ ዕለት ፓርላማው ወ/ሮ ገዳም ማንደፍሮን በምክትል ዋና ኦዲተርነት ሾሟል፡፡ የዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ማቋቋሚያ አዋጅ ሁለት ምክትል ዋና ኦዲተሮች እንዲኖሩት የሚደነግግ ሲሆን፣ ወ/ሮ ገዳም ማንደፍሮም ሁለተኛዋ ምክትል ዋና ኦዲተር ሆነው በፓርላማው ተሹመዋል፡፡
ወ/ሮ ገዳም በ1993 ዓ.ም. በቢዝነስ ኤጁኬሽን በዲፕሎማ፣ በማርኬቲንግ ማኔጅመንት በዲግሪ እንዲሁም በ2003 ዓ.ም. በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን የማስትሬት ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መያዛቸውን የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል፡፡