የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንና በሔኒከን ቢራ ፋብሪካ የሚጠመቀው ዋሊያ ቢራ ለአራት ዓመት የሚደርስ ስምምነት አደረጉ፡፡ እንደ ሪፖርተር ምንጮች ከሆነ የስፖንሰርሽፕ ስምምነቱ ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚሆን፣ ይህም ለሚቀጥሉት አራት ዓመታት የሚዘልቅ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ባለበት የፋይናንስ እጥረት ምክንያት አሁን ከዋሊያ ቢራ ጋር ያደረገው የስፖንሰርሽፕ ስምምነት ትልቅ ሥፍራ የሚሰጠው መሆኑን የሚናገሩት ምንጮች፣ ይህ ከዚህ ቀደም ያልታየ ከፍተኛ ገንዘብ የተመደበለት ስፖንሰርሽፕ ፌዴሬሽኑን ለበለጠ የፋይናንስ አማራጭ ከመሆኑ ጎን ለጎን የእግር ኳስ ቢዝነስ እንዲነቃቃ እንደሚያደርግ እምነት አላቸው፡፡
የቀድሞ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራር የብሔራዊ ቡድኑን የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎን መሠረት አድርጎ በፋይናንስ በኩል አቅሙን ለማጠናከር የተሻለ እንቅስቃሴ ማድረጉን የሚጠቁሙት እነዚሁ ምንጮች፣ ይኽኛው ግን ከቀድሞው አንፃር ደካማ ሆኖ መቆየቱን ይገልጻሉ፡፡ ያም ሆኖ አሁን የተደረገው ስምምነት ይበል የሚያሰኝና የፌዴሬሽኑን የፋይናንስ አቅም ለማጎልበት የሚረዱ ሌሎች ተመሳሳይ ስምምነቶችን እንዲያደርግ ዕድል እንደሚፈጥርለትም ይናገራሉ፡፡
ከዚህ ቀደም በአሁኑ ሔኒከን ቢራ ፋብሪካ ሥር የሚተዳደረው በደሌ ቢራ ዋሊያዎቹን ለሁለት ዓመት ስፖንሰር ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ በአጠቃላይ ስምምነቱ 24 ሚሊዮን ብር እንደነበር መዘገቡ የሚታወስ ነው፡፡ ይህ በፌዴሬሽኑና በዋሊያ ቢራ መካከል የሚደረገው የአራት ዓመት የስፖንሰርሽፕ ስምምነት ዛሬ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ሒልተን በይፋ ሥነ ሥርዓቱ የሚፈጸም መሆኑን ፌዴሬሽኑ አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል የኮካ ኮላ ካምፓኒ በአገሪቱ የትምህርት ቤቶችንና መሰል የፕሮጀክት ውድድሮች ለአምስት ዓመት በየዓመቱ አሥር ሚሊዮን ብር ስፖንሰር ለማድረግ ፍላጎት ቢኖረውም፣ በብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በኩል ነገሮች እየተጓተቱ መሆኑ የሪፖርተር ምንጮች ይገልጻሉ፡፡