ከ300 በላይ የሚሆኑ የአዲስ አበባ ከተማ ቴክኒክና ሙያ የግል ማሠልጠኛ ተቋማት ባለቤቶችና አሠሪዎች ማኅበር አቋቋሙ፡፡ ከአዲስ አበባ ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ እውቅና የተቸረው ይኸው ማኅበር፣ በግል የቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ተቋማት መካከል የሐሳብና የልምድ ልውውጦች የሚደረግበት፣ የግንኙነት መረብ በመዘርጋት ለትምህርት ሥልጠና ሥርዓቱ ስኬት የበኩሉን አስተዋጽኦ የሚያደርግበት መሆኑ ተገልጿል፡፡
የማኅበሩን መመሥረት አስመልክቶ መጋቢት 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተነገረው፣ በቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ዘርፍ የተገኙ ውጤቶችን ቀጣይነት ለማረጋገጥና የአገሪቱን የትምህርት ሥልጠና አገልግሎት ሽፋን ለማሳደግ መንግሥት የጀመረውን ለማጠናከር የተቋማቱ በማኅበር መደራጀት ወሳኝ ነው፡፡
ግርታን በሚፈጥሩ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመምከር የፈቃድ አሰጣጥ፣ የብቃት ማረጋገጫ ፈተና፣ ተጨማሪ እሴት ታክስ፣ የገቢ ግብር ታክስ የዕውቅና አሰጣጥ፣ የማሠልጠኛ ቤቶች ኪራይና የመሳሰሉት ጉዳዮች ከመንግሥትና ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ተቋማቱን ሲያጋጩ ከርመዋል፡፡
መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት የሚያወጣቸው መመሪያዎችና ፖሊሲዎች አፈጻጸም ላይም ችግሮች አሉ፡፡ ይህንኑ ችግር ለመቅረፍና የግል ተቋማትን መብትና ጥቅም ለማስጠበቅ የግል ቴክኒክና ሙያ ተቋማት ማኅበር መቋቋሙን መግለጫው አመልክቷል፡፡
የግል ቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ተቋማት በቴክኒክና ሙያ ኤጀንሲ በሚወጡ ፖሊሲዎች፣ ሕጎችና ደንቦች ላይ በመሳተፍ አስተያየት በመስጠትና ክፍተቶቹን በመሙላት አስተዋጽኦ ማድረግ፣ በፖሊሲዎች፣ በሕጎችና በደንቦች ዙሪያ የአባላት ግንዛቤ እንዲዳብር ትምህርት መስጠት፣ ዘርፉን ለማጠናከር የሚያስችል የፋይናንስ ድጋፍ እንዲያገኙ፣ መሥሪያ ቦታ፣ ብድር፣ ዋስትና ማመቻቸትና ማፈላለግ ከማኅበሩ ዓላማዎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡
በራስ አምባ ሆቴል አዳራሽ በተከናወነው በዚህ ሥነ ሥርዓት ላይ የኢትዮጵያ አሠሪዎች ፌዴሬሽን፣ የአዲስ አበባ የሙያ ብቃት ምዘናና ማረጋገጫ ማዕከል፣ የአዲስ አበባ ቴክኒክና ሙያ ትምህርት ኤጀንሲ፣ የአዲስ አበባ ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ለማኅበሩ ያላቸውን አጋርነት በየተራ ገልጸዋል፡፡ ማኅበሩን በፕሬዚዳንትነት የሚመሩት አቶ ነጋሲ አርአያ ናቸው፡፡