Tuesday, November 28, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊኢንዱስትሪ ዞን አልሚዎችን የሚቆጣጠር ድርጅት እንዲቋቋም ተወሰነ

ኢንዱስትሪ ዞን አልሚዎችን የሚቆጣጠር ድርጅት እንዲቋቋም ተወሰነ

ቀን:

የቻይና ኩባንያ ለሚያቋቁመው ኢንዱስትሪ ዞን የመሠረት ድንጋይ ሊቀመጥ ነው

   ከጥቂት ዓመታት ወዲህ እየተስፋፉ የሚገኙትን ኢንዱስትሪ ዞኖች የሚቆጣጠር ተቋም እንዲቋቋም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ውሳኔ አሳለፈ፡፡ በመንግሥትና በግል ባለሀብቶች እየተቋቋሙ የሚገኙ ኢንዱስትሪ ዞኖችን የሚቆጣጠረውን ተቋም እንዲያደራጅ ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡

      የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር መብራህቱ መለስ እንደገለጹት፣ መንግሥት ያቋቋመው የኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ኮርፖሬሽን ኢንዱስትሪ ዞኖችን እያለማ ነው፡፡ ‹‹የውጭ ኩባንያዎችም ኢንዱስትሪ ዞኖችን እያለሙ ነው፡፡ እነዚህን የኢንዱስትሪ ዞኖች የሚቆጣጠርና የሚያስተዳድር መንግሥታዊ ተቋም የሚያስፈልግ መሆኑ ታምኖበታል፤›› በማለት ዶ/ር መብራቱ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

በዶ/ር አርከበ እቁባይ አመራር የሚሰጠው የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ኮርፖሬሽን፣ በአምስት ከተሞች ኢንዱስትሪ ፓርኮችን በማቋቋም ላይ ይገኛል፡፡ በተለይ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሌሎች ተጨማሪ ኢንዱስትሪ ዞኖችን ለመገንባት ከአማካሪ ድርጅቶች ጋር ባለፈው መጋቢት 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ስምምነት ተፈርሟል፡፡ ስምምነቱን በዋነኛነት የፈረሙት ግንባታውን ለማካሄድ የወጣውን ጨረታ ከተሳተፉ 20 ኩባንያዎች ውስጥ አሸናፊ የሆኑት አራት ኩባንያዎች ናቸው፡፡ አሸናፊ የሆኑት ኩባንያዎች የደቡብ ኮሪያዎቹ ዶሃና ጀንግሊም፣ የህንዱ አይፒኢ ግሎባልና አገር በቀል ኩባንያ የሆነው መታፈሪያ ኮንሰልቲንግ ኢንጂነርስ ናቸው፡፡ ሥራው የሚካሄደው በጥምረት ሲሆን፣ ጥምረቱን ዶሃ ይመራዋል፡፡ የስምምነት ፊርማው ባለፈው ረቡዕ በዶ/ር መብራቱና የዶሃ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኪሞ ሐዮንግ ቡክ ተፈርሟል፡፡

እነዚህ ኩባንያዎች በዋነኛነት የሚያካሂዱት በአዲስ አበባ ቦሌ ለሚ አካባቢ ተጨማሪ የኢንዱስትሪ ዞን፣ ቂሊንጦ አካባቢም እንዲሁ አዲስ የኢንዱስትሪ ዞን መገንባት የሚያስችል ዝርዝር ዲዛይን ሥራ ማካሄድ ነው፡፡ ከዚህ ሥራ በተጨማሪ ኮንትራክተር በመምረጥ በኩል የጨረታ ሰነድ የሚያዘጋጁ ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ግንባታውን የመቆጣጠር ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል፡፡

የቦሌ ለሚ ቁጥር ሁለት ኢንዱስትሪ ዞን 86 ሔክታር ስፋት አለው፡፡ ለዚህ ፕሮጀክት ለዲዛይንና ለግንባታ የሚሆን ገንዘብ መገኘቱ ተገልጿል፡፡ የቂሊንጦ ፕሮጀክት ዲዛይን ገንዘብ የተገኘለት ቢሆንም፣ ለግንባታ የሚሆነው ገንዘብ እየተፈለገ መሆኑ ታውቋል፡፡ ለእነዚህ ፕሮጀክቶች የዓለም ባንክ 139 ሚሊዮን ብር ፋይናንስ አድርጓል፡፡ መንግሥት ከእነዚህ ኢንዱስትሪ ዞኖች በተጨማሪ በቅርቡ መቐለና ኮምቦልቻ ላይ ኢንዱስትሪ ዞኖችን ለማቋቋም የመሠረት ድንጋይ አስቀምጧል፡፡ ድሬዳዋና ሐዋሳ ላይ ወደ ግንባታ የተገባ ሲሆን፣ ቀደም ሲል አዲስ አበባ ቦሌ ለሚ የተገነባው ኢንዱስትሪ ዞን ግንባታው ተጠናቆ በርካታ የውጭ ኩባንያዎች ፋብሪካዎቻቸውን እየከፈቱ መሆናቸው ታውቋል፡፡

ዶ/ር መብራቱ እንደገለጹት፣ በግል ባለሀብቶችም በርካታ የኢንዱስትሪ ዞኖች እየተገነቡ ነው፡፡ የባንግላዴሽ ኩባንያ ቢዲኤል መቐለ ከተማ 80 ሔክታር መሬት ተረክቧል፡፡ በዚህ ቦታ ላይ ኢንዱስትሪ ዞን እንደሚያለማ ተገልጿል፡፡ የቻይናው ግዙፍ ኩባንያ ሁጂያን ዱከም አካባቢ በሚገኘው ኢስተርን ኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ በከፈተው የጫማ ፋብሪካ በወር 1.3 ሚሊዮን ጥንድ ጫማዎች ያመርታል፡፡ ይህ ግዙፍ ኩባንያ የራሱን የኢንዱስትሪ ዞን ለማቋቋም ከአዲስ አበባ አስተዳደር ቦሌ ለሚ አካባቢ 138 ሔክታር መሬት ተረክቧል፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት የመሠረት ድንጋይ እንደሚቀመጥ ዶ/ር መብራቱህ ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቱ እውን ሲሆን የኩባንያው ኢቨስትመንት በአጠቃላይ 2.2 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ ተገልጿል፡፡

የታይዋን ኩባንያ ጀርጂሹ ኮርፖሬሽን በጫማ ማምረት ሥራ የተሰማራ ሲሆን፣ በቀን 4,000 ጥንድ የሴት ጫማዎች ያመርታል፡፡ ይህ ኩባንያ ሞጆ ከተማ የራሱ ኢንዱስትሪ ዞን ለማቋቋም መቶ ሔክታር መሬት ተረክቧል፡፡ የግብፅ ባለሀብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ ቀደም ብሎ በገባው ኤልስዌዲ በኩል 400 ሔክታር መሬት እንዲሰጣቸው መጠየቁን ዶ/ር መብራቱህ ተናግረዋል፡፡ በዚህ መሬት ላይ ዘመናዊ የኢንዱስትሪ ዞን መገንባት እንደሚፈልጉ የተናገሩት ዶ/ር መብራህቱ፣ ‹‹ህንዶችም በዚህ ዘርፍ ለመሰማራት ፍላጎት አሳይተዋል፤ ቱርኮችም ወደ ግንባታ ገብተዋል፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር መብራቱ እንዳሉት የኢንዱስትሪ ዞን ለማቋቋም በርካታ ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በተሻሻለው የኢንቨስትመንት አዋጅ የግል ኩባንያዎች ከመንግሥት ጋር በሽርክና ማልማት ከፈለጉ በሩ ክፍት እንዲሆን ተደርጓል፡፡  

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለሲኒመር ትሬዲንግ አ/ማ አባላት በሙሉ የጠቅላላ ጉባኤ የስብሰባ ጥሪ

ለሲኒመር ትሬዲንግ አ/ማ አባላት በሙሉ የጠቅላላ ጉባኤ የስብሰባ ጥሪ ሲኒመር ትሬዲንግ...

የባህር በር በቀጣናዊ ተዛምዶ ውስጥ

በበቀለ ሹሜ መግቢያ በ2010 ዓ.ም. መጋቢት ማለቂያን ይዞ ዓብይ አህመድ በጠቅላይ...

ሥጋት ያስቀራል ተብሎ የሚታሰበው የጫኝና አውራጅ መመርያ

በአዲስ አበባ ከተማ በሕገወጥ መልኩ በመደራጀት ማኅበረሰቡ ላይ እንግልትና...

ማወቅ ወይስ አለማወቅ – ድፍረት ወይስ ፍርኃት?

በአሰፋ አደፍርስ ወገኖቼ ፈርተንም ደፍረንም የትም አንደርስምና ለአገራችን ሰላምና ክብር...