‹‹እየደረሰባችሁ ያለውን ሰቆቃ ለመገንዘብ ከባድ ቢሆንብንም ፈፅሞ አንዘነጋችሁም፡፡›› የ17 ዓመቷ ፓኪስታናዊት የኖቤል የሰላም ሽልማት ተሸላሚዋ ማላላ ዩሳፍዛይ፣ የዛሬ ዓመት በናይጄሪያ የሽብር ቡድን ቦኮ ሐራም የታገቱትን 200 ልጃገረዶች አስመልክቶ የተከናወነውን የመታሰቢያ ሥነ ሥርዓት አስመልክታ ከጻፈችው ደብዳቤ የተወሰደ፡፡ ፓኪስታን ውስጥ በሚንቀሳቀሰው ታሊባን ጭንቅላቷን በጥይት ተመታ እንግሊዝ ውስጥ በተደረገላት ከፍተኛ የሕክምና ዕርዳታ ሕይወቷ የተረፈው ታዳጊ፣ በቦኮ ሐራም የታገቱት ልጃገረዶች በናይጄሪያ መንግሥት መሪዎችና በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ችላ ተብለዋል ብላለች፡፡ እሷም እንደ በርካታ ተቆርቋሪ ሰዎች ልጃገረዶቹ ከቦኮ ሐራም ሰቆቃ እንዲላቀቁ ጫና እንደምትፈጥር ተናግራለች፡፡ ‹‹ደፋሮቹ እህቶቼ›› ያለቻቸውን የታገቱ ልጃገረዶች ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጠንክሮ ማስለቀቅ አለበት ብላለች፡፡ ‹‹እናንተ ደፋር እህቶቼ እናንተን አግኝቼ የማቅፍበት፣ አብሬያችሁ የምፀልይበትና ከቤተሰቦቻችሁ ጋር ነፃነታችሁን የማከብርበት ቀን ናፍቆኛል፤›› በማለት አጋርነቷን ገልጻለች፡፡ በምሥሉ ላይ የምትታየው ታዳጊዋ የኖቤል የሰላም ሽልማት አሸናፊዋ ማላላ ዩሱፍዛይ ናት፡፡