በኪነ ጥበቡ ታዋቂ የሆኑ ግለሰቦች፣ በመገናኛ ብዙኃን ያስተዋውቁት የነበረው የፅሑፍ መልዕክት መላኪያ 8100 ኤ፣ ለታላቁ ህዳሴ ግድብ የተጣራ 84 ሚሊዮን ብር ገቢ እንዳስገኘ ታወቀ፡፡ ባለፈው ስድስት ወር በሦስት ብር ክፍያ ‹‹ኤ›› ፊደልን ከተንቀሳቃሽ ስልኮቻቸው የላኩ ግለሰቦች በርካታ ስለነበሩ ገቢው እንደጨመረ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሔራዊ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተሩ አቶ ፈቃዱ ከተማ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ በ8100 ኤ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ካደረጉ ድርጅቶች መካከል በአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪና በኤሌክትሮኒክስ ዘርፍ ያሉ ባለሀብቶች ይጠቀሳሉ፡፡ ኢኳቶሪያል ቢዝነስ ግሩፕ፣ ማራቶን ሞተርስ ኢትዮ ኒኮንና ሌሎችም በመኪና ኢንዱስትሪ ያሉ ድርጅቶች እስከ 1.5 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ መኪናዎችን አበርክተዋል፡፡
በተጨማሪ ስናፕ፣ አልታ፣ ሀሮን ኮምፒዩተርና ሌሎችም ድርጅቶች ለሽልማት የሚሆኑ ላፕቶፖችን ሰጥተዋል፡፡ አቶ ፈቃዱ ሪፖርተርን ጨምሮ ልዩ ልዩ ሚዲያዎችን 8100 ኤን በማስተዋወቅ እንዲሁም የኢትዮጵያ ቴሌኮምዩኒኬሽን በነፃ አጭር መልዕክት በመላክና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በነፃ በማስተላለፍ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ብለዋል፡፡
የተጠቀሱትን ተቋሞች ጨምሮ 1,200 ተቋሞች ለግድቡ ላበረከቱት አስተዋጽኦ የምሥጋና መርሐ ግብር ሚያዝያ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. በሒልተን አዲስ ተካሂዷል፡፡ የታላቁ ህዳሴ ግድብ የመሠረት ድንጋይ የተቀመጠበትን አራተኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በተሰናዳው ዝግጅት፣ ሽልማት የተሰጣቸው ለግድቡ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ እንደሆኑ ተገልጿል፡፡
ሥነ ሥርዓቱ ላይ ተገኝተው ሽልማት ያበረከቱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሔራዊ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ደመቀ መኰንን፣ ‹‹ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በመሰለ የሕዝብ ሕይወትና የአገር ገጽታ በሚቀይር ታሪካዊ ፕሮጀክት ላይ መሳተፍ በራሱ ሽልማት ቢሆንም፣ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉትን መሸለም አስፈላጊ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ግድቡ አሁን ካለበት ወሳኝ ደረጃ ላይ እንዲደርስ ሕዝቡ ላደረገው አስተዋጽኦ ምሥጋና አቅርበዋል፡፡ በገንዘብ፣ በፐብሊክ ዲፕሎማሲ፣ በአካባቢ ጥበቃና በሌላም መንገድ የሚደረገው ድጋፍ እንዲቀጥልም መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
አቶ ፈቃዱ በበኩላቸው፣ ‹‹ሽልማቱ በሀብት፣ በጉልበትና በዕውቀት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ተሰጥቷል፡፡ በእርግጥ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በግድቡ ላይ ለነበረው ተሳትፎ ሽልማት ይገባዋል፡፡ ዕውቅናው መሰጠቱ ለተሸላሚዎች የሞራል ጥንካሬ የሚሰጥና ሌሎችንም ለተመሳሳይ ሥራ የሚያነሳሳ ይሆናል፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
8100 ኤ ቦንድ መግዛት የማይችሉ ግለሰቦችንም በግድቡ ሥራ እንዲሳተፉና ግድቡ የጋራ አጀንዳ ሆኖ በሕዝብ ልብ እንዲቆይ አስችሏል ብለዋል፡፡ በማስተዋወቅ ሥራው የተሳተፉ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችን ‹‹የግድቡ የጀርባ አጥንት›› በማለት ገልጸው፣ ሕዝቡን ያነሳሱ ሥራዎችን እንዳቀረቡ ተናግረዋል፡፡
በሽልማቱ ከተካተቱ መካከል የተለያዩ የሙያ ማኅበራት፣ ግለሰቦች፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ይጠቀሳሉ፡፡ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር፣ ሰርከስ ኢትዮጵያ፣ የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን፣ የአዲስ አበባ መምህራን ማኅበር፣ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ጽሕፈት ቤትና ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ከተሸላሚዎቹ መካከል ናቸው፡፡ በተጨማሪ ባንኮች፣ ሙዚቀኞች፣ ኮሜዲያን፣ አትሌቶች፣ የማስታወቂያ ሥራ ድርጅቶች፣ ጥናታዊ ጽሑፎችን ያዘጋጁ ግለሰቦች፣ ባለሀብቶች እንዲሁም የሚዲያ ተቋሞች ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
8100 ኤ ከጥቂት ጊዜ በኋላ እንደሚጀመርና በቅርብ 14 ዘፈኖች የያዘ የሙዚቃ አልበም ለግድቡ የሚውል ገቢ ለማስገኘት ለገበያ እንደሚቀርብ ለማወቅ ተችሏል፡፡