ምናልባት በጥሩነሽ ዲባባ የአነጋጋሪ ብቃት ልቡ የነሆለለ ኢትዮጵያዊ በወላጅ እናታቸው ማሕፀን ውስጥ ‹‹ገንዘቤ›› የምትባል ሌላ አነጋጋሪ እንስት ትፈጠራለች ብሎ መገመቱ ያጠራጥራል፡፡ በእርግጥ እጅጋየሁ ዲባባም ከዚሁ ማሕፀን መገኘቷ ሌላ ተስፋን ለመሰነቅ አንድ ምክንያት ይሆናል፡፡ ትልቋ ጥሩነሽ ከቤጂንግ እስከ ኤድመንተን፣ ከዚያም እስከ ለንደን በአንፀባራቂ ድል የአገራችን ሰንደቅ ዓላማ ከፍ አድርጋ ስታስጠራ ሥጋዋ የሆነችውን ታናሽ እህቷንም በተጠባባቂ ዙፋን ላይ አስቀምጣት እንደነበር ብዙ ሰው ልብ አላለው ይሆናል፡፡ የሆነው ሆኖ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በክስተትነት ብቅ ያለችው ትንሿ ገንዘቤ የኢትዮጵያ ሕዝብ በዲባባ ቤተሰብ ላይ ሌላ ተስፋን እንዲሰንቅ አድርጋዋለች፡፡ ባለፈው የፈረንጆች ዓመትም በ1,500 ሜትርና በ3,000 ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር የዓለም ሪከርድን ከሰባበረች በኋላ የዓለምን መገናኛ ብዙኃን ቀልብ ስባለች፡፡ ይኼንን ተከትሎም ዓለማቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር (አይኤኤኤፍ) የዓመቱ ምርጥ እንስት ስፖርተኛ ሲል አንግሷታል፡፡ ከገንዘቤ ጋር በዘርፉ የተፎካከረችውን ኒውዝላንዳዊት አሎሎ ወርዋሪዋ ቫሌሪ አዳምስ በሁለተኛነት ፉክክሩን ስታጠናቅቅ፣ ገንዘቤ ከአሜሪካዊቷ የሜዳ ቴኒስ ስፖርተኛ ሴሬና ዊሊያምስ ጋር የዓመቱ ምርጥ እንስት ስፖርተኞች ዝርዝር ውስጥ ተካታለች፡፡ እንደ አብዛኛው የመገናኛ ብዙኃን ሽፋን ገንዘቤ ይህ የሚገባት መሆኑና በቀጣይም አሁን የምትገኝበት ወቅታዊ አቋም ለሌላ ተመሳሳይ ክብር ሊያበቃት እንደሚችልም ዘግበዋል፡፡ የ23 ዓመቷ ገንዘቤ ዲባባ እስካሁን በምትታወቅበት የአጭርና የመካከለኛ ሩጫ ውጤታማነት በተለየ መልኩ በረዥም ርቀት ሩጫዎች ላይም ተካፋይ በመሆን ሌላ ክብርን መቀዳጀት እንደምትፈልግ ቀደም ሲል የገለጹት ሲሆን፣ ይህም አገሪቱ በእነ ጥሩነሽ ዲባባ ወደ ጎዳና ውድድር ማዘንበል ምክንያት ሊገጥማት የሚችለውን ክፍተት እንደሚሞላላት ይገመታል፡፡ ባለፈው የፈረንጆች ዓመት በሞሮኮዋ ማራካሸ በተካሄደው የዓለም 1,500 ሜትርና 3,000 ሜትር ሻምፒዮና የተቀዳጀችውን አንፀባራቂ ድልና ያስመዘገበችው አዲስ ሪከርድ እንዳለ ሆኖ፣ በጎልደን ሊግና በሌሎችም ውድድሮች ገንዘቤ እጅግ በጣም ጥሩ ውጤትን ማስመዝገቧ የዓመቱ ምርጥ እንስት ስፖርተኝነት ሽልማቱ የሚገባት ስለመሆን ብዙዎችን የሚያስማማ መሆኑ ተዘግቧል፡፡