በሁለተኛው አገር አቀፍ ስፖርት ኤግዚቢሽንና ባዛር ከዓምናው ተሳታፊዎች በላይ በርካታ የስፖርት ዘርፍ ባለሀብቶችና የስፖርት ማኅበራት እንደሚገኙ ተገለጸ፡፡
ከሰኔ 9 እስከ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የስፖርት ማኅበራት፣ በኢትዮጵያ የስፖርት ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች፣ ፌዴሬሽኖች፣ ክለቦችና እንዲሁም የተለያዩ ባለድርሻ አካላት እንደሚሳተፉ በብሔራዊ ሆቴል ሚያዝያ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. አዘጋጆቹ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ታውቋል፡፡
ኤግዚቢሽንና ባዛሩ በጂኤም ኤስ ማስታወቂያ ሥራና ፈለቀ ደምሴ ኮሙዩኒኬሽን ፕሬስ ሥራዎች በጋራ የሚዘጋጅ ሲሆን፣ በወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ዕውቅናና ድጋፍ እንደተደረገላቸው የጂኤምኤስ አድቨርታይዚንግ ሥራ አስኪያጅና የሕግ አማካሪ አቶ ዘለዓለም ፍሥሐ ተናግረዋል፡፡
በኤግዚቢሽኑ የተለያዩ የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች አዳዲስ ደጋፊዎችን የሚያገኙበት መድረክ መፍጠር፣ ክለቦች የተለያዩ ቁሳቁሶችን ማቅረብ፣ በስፖርቱ ዘርፍ ትልቅ ዝናና ታሪክ ያላቸውን ሰዎች በማስተዋወቅና ተጠቃሚ የሚያደርጋቸው ዕድል እንደሚፈጥር የኮሙዩኒኬሽን የፕረስ ሥራዎች ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ፈለቀ ደምሴ አብራርተዋል፡፡
የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ተወካዩ አቶ መኰንን ይደርሳል በበኩላቸው፣ ‹‹በስፖርቱ በዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶች፣ ፌዴሬሽኖችና የስፖርት ማኅበራት አንድ ላይ በመሆን የስፖርት ኢንቨስትመንት ማስፋፋት ይኖርባቸዋል፤›› ብለዋል፡፡
በተጨማሪም በሌሎች የስፖርት ዘርፍ ላይ የተሰማሩ እንደዚህ ዓይነት መንገድ መከተል እንዳለባቸው፣ እስካሁን ባለው መረጃ መሠረት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን፣ ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴና የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሔራዊ አካዴሚን ጨምሮ ስድስት የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ተሳታፊ እንደሚሆኑ በመግለጫው ተነግሯል፡፡