የአገር ውስጥ ፍላጎትን ሙሉ ለሙሉ ለማርካትና በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ድርሻ ለመያዝ የተጀመረው የስኳር ልማት ዘርፍ፣ ከወዲሁ በተለያዩ ችግሮች በመተብተቡ መንግሥት 115 ሺሕ ሔክታር መሬት ተቀንሶ ለጥጥ ልማት እንዲውል ወሰነ፡፡
በዚህ ውሳኔ መሠረት በደቡብ ክልል ከሚገኘው ደቡብ ኦሞ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝና በአማራ ክልል ከሚገኘው ጣና በለስና በኦሮሚያ ክልል ከሚገኘው አርጆ ደዴሳ ስኳር ልማት ፕሮጀክቶች መጠኑ የተገለጸው መሬት ተቀንሶ ለጥጥ ልማት እንዲውል መወሰኑን የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት የ2009 በጀት ዓመት የሰባት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ይገልጻል፡፡
የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ስለሺ ለማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ለጥጥ ልማት የሚሆኑ ቦታዎች እየተለዩ የዳሰሳ ጥናት ተደርጎባቸዋል፡፡
በሚኒስትሮች ምክር ቤት ውሳኔ በ2003 ዓ.ም. የተቋቋመው የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን፣ ነባሮቹን ሦስት ስኳር ፋብሪካዎች (ወንጂ ሸዋ፣ መተሐራና ፊንጫ) ሳይጨምር፣ አሥር ስኳር ፋብሪካዎችን በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ወጪ የማቋቋም ዕቅድ አውጥቷል፡፡
በአማራና በቤንሻንጉል ጉሙዝ በጣና በለስ ስኳር ልማት ፕሮጀክት 50 ሺሕ ሔክታር መሬት ለማልማትና በቀን 12 ሺሕ ቶን አገዳ ለመፍጨት የሚችሉ ሁለት ፋብሪካዎች፣ በደቡብ ክልል በደቡብ ኦሞ ዞን፣ ቤንች ማጂና ከፋ ዞኖች፣ በኦሞ ኩራዝ እያንዳንዳቸው 12 ሺሕ ቶን አገዳ የመፍጨት አቅም ያላቸው፣ እንዲሁም በቀን 24 ሺሕ ቶን አገዳ የመፍጨት አቅም ያለውን አንድ ፋብሪካ በድምሩ የአራት ፋብሪካዎች ግንባታ እየተካሄደ ነው፡፡
በምዕራብ ኢትዮጵያ በኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ ወለጋ፣ ኢሉአባቦራና በጅማ ዞኖች የሚገኘው አርጆ ደዴሳ ስኳር ፕሮጀክትም የዚሁ ግዙፍ ዕቅድ አካል ነው፡፡
መንግሥት በያዛቸው በእነዚህ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የአገሪቱን የስኳር ፍላጐት በማርካት፣ የሚመረተውን ምርትም ወደ ውጭ በመላክ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ለማስገኘት አቅዷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም 31,341,000 ሊትር ኢታኖል ማምረትም የዕቅዱ አካል ነው፡፡ በአጠቃላይ ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን ሲጠናቀቅ (2012 ዓ.ም.) 307,324 ሔክታር መሬት በሸንኮራ አገዳ ለመሸፈን ታቅዷል፡፡
ነገር ግን ዕቅዱ በተለያዩ ችግሮች ምክንያት በታሰበው መጠንና ጊዜ መጓዝ ሳይችል ቀርቷል፡፡ ዘርፉ ከፍተኛ በጀት የሚፈልግ በመሆኑ፣ ፕሮጀክቶቹን ለማካሄድ የታቀደባቸው ቦታዎች የመሠረተ ልማት ያልተሟላላቸው በመሆናቸውና በርካታ የስኳር ልማት ፕሮጀክቶች በታቀደላቸው ጊዜ ውስጥ መካሄድ እንዳልቻሉ ሲገለጽ ቆይቷል፡፡ መንግሥት በስኳር ዘርፍ ቀደም ብሎ በያዘው ዕቅድ ላይ ማስተካከያ በማድረግ፣ በዘርፉ ለመሰማራት ለሚፈልጉ ኩባንያዎችም በሩን ክፍት አድርጓል፡፡ ማስተካከያው በጥልቀት በመደረጉም የስኳር ልማት መሬት እንዲቀንስ ተደርጐ ለጥጥ ልማት እንዲውል ተወስኗል፡፡
የስኳር ፕሮጀክትና ይፋ በተደረጉበት ወቅት በአፋር ክልል የሚገኘውና የጥጥ እርሻ የነበረው የተንዳሆ እርሻ ልማት ድርጅት መሬት፣ ለስኳር ልማት እንዲውል መደረጉ ይታወሳል፡፡
በጥጥ ልማት በኩል እስካሁን ድረስ 78 ሺሕ ሔክታር መሬት በጥጥ ተሸፍኗል፡፡ የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት የካቲት 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ይፋ ባደረገው የሰባት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት፣ በጥጥ የሚሸፈነውን መሬት ወደ 250 ሺሕ ሔክታር ለማድረስ መታቀዱን ገልጿል፡፡
በኢትዮጵያ በርካታ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች እየተከፈቱ በመሆናቸው፣ ለእነዚህ ፋብሪካዎች ዋነኛ ጥሬ ዕቃ የሆነውን ጥጥ በብዛት ለማምረት ታቅዷል፡፡