ባለፈው ሳምንት የካቲት 18 ለ19 ቀን 2009 ዓ.ም. አጥቢያ ከሌሊቱ 9፡30 ሰዓት ላይ፣ የ32 ዓመት ጣሊያናዊ ወጣት በጥይት መትቶ ገድሏል የተባለውን ተጠርጣሪ ፖሊስ በቁጥጥር ሥር ማዋሉን አስታወቀ፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ለሪፖርተር እንደገለጸው፣ ሟች ጃማ ካርሎስ ጉላን ገድሏል ተብሎ የተጠረጠረው ግለሰብ ብሩክ ጫኔ ይባላል፡፡ ገዳዩም በሰላሳዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ ወጣት መሆኑን የገለጸው ፖሊስ፣ የግድያውን መንስዔ በማጣራት ላይ መሆኑን ተናግሯል፡፡
ወጣቱ ተጠርጣሪ ግድያውን ስለመፈጸሙ ሙሉ በሙሉ በእምነት ቃሉ ማረጋገጡንም ፖሊስ ገልጿል፡፡ ፖሊስ ጣሊያናዊው ወጣት በተገደለበት ዕለት በቁጥጥር ሥር ካዋላቸው ተጠርጣሪዎች መካከል ወጣት ብሩክ አብሮ ታስሮ እንደነበርም ገልጿል፡፡ በወቅቱ ገዳዩን መለየት ባይቻልም ሰሞኑን በተደረገ ምርመራ፣ ከተጠርጣሪዎቹ አንዷ ስለግድያውና ማን እንደገደለው በመናገሯ ብሩክም ሲጠየቅ ማመኑን ፖሊስ አስረድቷል፡፡
ሟች ስልክ ደውሎ ካለበት ቦታ እንዲመጣለት እንደጠየቀና እሱም ካለበት ቦታ ድረስ ሄዶ ሲደውልለት ከነበረበት መዝናኛ ቦታ ወጥቶ መምጣቱን፣ በመሪው በኩል ሆኖ ሲታገለው የያዘውን ሽጉጥ እያሳየ ተው እመታሃለሁ እያለው ሲላፋ በድንገት ምላጩ ተስቦ እንደመታው ቃል መስጠቱን ፖሊስ ገልጿል፡፡
በመሆኑም የገደለበትን ሽጉጥና ሲያሽከረክር የነበረውን ቢኤም ደብልዩ መኪና በቁጥጥር ሥር አድርጎ ምርመራውን መቀጠሉንና ለግድያ የሚያበቃ ተጨማሪ ነገር ካለ በቀጣይ ምርመራ ማወቅ እንደሚችል ፖሊስ ገልጿል፡፡