ዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ፀረ ባክቴሪያን (አንቲባዮቲክ) የተለማመዱ 12 ቤተሰቦች ያሏቸውን የባክቴሪያ ዓይነቶች ይፋ አደረገ፡፡ ድርጅቱ በድረ ገጹ እንዳሰፈረው፣ አንቲባዮቲክ የተላመዱት አሲኒቶባክተር፣ ሲዶማናስ፣ ክላብሲያላ፣ ኢኮሊ፣ ሴሬዥያና ፕሮቲየስ የተባሉት ባክቴሪያዎች ናቸው፡፡
በሆስፒቴሎች፣ በቤት ውስጥ አስታማሚዎች እንዲሁም በሰው ልጆች ጤና ላይ ከፍተኛ አደጋ ተጋርጧል ያለው ድርጅቱ፣ አያይዞም አዳዲስ አንቲባዮቲኮች ባስቸኳይ እንደሚያስፈልጉ ገልጿል፡፡
መድኃኒቶችን የተለማመዱት ባክቴሪያዎች ገዳይ የሆኑ፣ እንደ ኒሞኒያና ደም በሚዘዋወርባቸው የሰውነት ክፍሎች ውስጥ የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖችን የሚያስከትሉ ናቸው፡፡
ባክቴሪያዎቹ ብዙ ፀረ ባክቴሪያዎችን የተለማመዱ ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም መድኃኒት ለተለማመዱ ባክቴሪያዎች ይውሉ የነበሩትን ካርባፕነምሳና ሦስተኛው ትውልድ ሴፎሃሎስፓሪንስን ጭምር መለማመዳቸው ለጤናው ዘርፍ አስደንጋጭ መርዶ ነው፡፡ እንደ ጨብጥና ምግብ መመረዝን የመሰሉ የተለመዱ በሽታዎችን የሚያክሙ ፀረ ባክቴሪያዎችም የተለማመዱ ናቸው ተብሏል፡፡ ከዚህ ቀደምም ቲቢ መድኃኒት መለማመዱ መገለጹ ይታወቃል፡፡
ድርጅቱ ጀርመን ከሚገኘው ቱቢኒን ዩኒቨርሲቲ ኢንፌክሽን አመንጪ በሽታዎች ክፍል ጋር በመተባበር ባክቴሪያዎቹን የለየ ሲሆን፣ በአፋጣኝም አዳዲስ መድኃኒቶች እንደሚያስፈልጉ አሳውቋል፡፡
‹‹አዳዲስ መድኃኒቶች መሠራታቸው በእነዚህ ባክቴሪያዎች ምክንያት የሚከሰተውን ሞት ለመቀነስ ያስችለናል፤›› ሲሉም በዩኒቨርሲቲው በኢንፌክሽን የሚከሰቱ በሽታዎች ክፍል ኃላፊ ፕሮፌሰር ኢቭሊና ታኮኔል ገልጸዋል፡፡