ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) አመራሮች መካከል ከገዥው ፓርቲ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ጋር እየተደረገ ባለው ድርድር ምክንያት አለመግባባት መፈጠሩን፣ የፓርቲው የጥናትና ምርምር ኃላፊ አቶ ዋስይሁን ተስፋዬ ለሪፖርተር ገለጹ፡፡
አቶ ዋስይሁን ይኼን የገለጹት በድርድሩ ሒደት ደስተኛ ያልሆኑ የፓርቲው አባላት የፓርቲውን ፕሬዚዳንት ጫኔ ከበደ (ዶ/ር) አንስተው፣ አቶ አዳነ ታደሰን ፕሬዚዳንት አድርገው መምረጣቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ ማሠራጨታቸውን ተከትሎ ነው፡፡
‹‹ድርድሩን በሚመለከት በፓርቲው ውስጥ የተፈጠረ ልዩነት አለ፡፡ ነገር ግን ፓርቲው በድርድሩ ቀጥሏል፡፡ ፓርቲው በድርድሩ መቀጠል የለበትም የሚል አካል ወይም ግለሰብ ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን ይኼ አካል መብቱን ወይም ፍላጎቱን ማሳካት ያለበት በሕገወጥ መንገድ አይደለም፤›› በማለት በአቶ አዳነ ታደሰ ፕሬዚዳንትነት የወጣው ደብዳቤ ሕገወጥ እንደሆነ አቶ ዋስይሁን አስታውቀዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም የወቅቱ የኢዴፓ ፕሬዚዳንት በፓርቲው የምርጫ ሥርዓትና ሒደት የተመረጡ መሆናቸውን አስታውቀው፣ ‹‹የፓርቲው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ መሥፈርት ባልተሟላበት ሁኔታ ማንም ሰው በእጁ ላይ በአጋጣሚ ማኅተም ስላገኘ ብቻ፣ ፕሬዚዳንት ነኝ እያለ የፈለገውን ውሳኔ ማሳለፉ ወንጀል ነው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡
ስለሆነም የፓርቲው አባላት የፓርቲውን ማኅተም ያላግባብ በመጠቀማቸው ፓርቲው ክስ እንደመሠረተና ወንጀሉን የሚያጣራው አካል የማጣራት ሥራውን እያከናወነ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
በደብዳቤው ሕገወጥነት ላይ አፅንኦት ሰጥተው የተናገሩት አቶ ዋስይሁን፣ ‹‹አዳነ ደብዳቤ ጽፎና ማኅተም አድርጎ ፓርቲውን ከድርድሩ ሊያስወጣ አይችልም፡፡ በዚህም ምክንያት ፓርቲው ከድርድሩ አልወጣም፡፡ እርሱ ግን ይኼን በመጻፉ ይጠየቃል፤›› ብለዋል፡፡
በአቶ አዳነ ታደሰ ፊርማ የወጣው ደብዳቤ ፓርቲውን የማይወክሉ ሰዎች በድርድሩ እየተሳተፉ እንደሆነ በመጥቀስ፣ በዚህ ምክንያት በድርድሩ ላይ እየተወሰኑ ያሉ ውሳኔዎችን ፓርቲው የማያውቃቸው እንደሆኑ ይገልጻል፡፡ ‹‹ከዚህም በኋላ በ13/02/2010 ዓ.ም. ፓርቲው በደብዳቤ ያሳወቃቸውን ተወካዮች ተቀብላችሁ ድርድሩ ላይ ተሳትፎ እንድናደርግ ካላደረጋችሁ፣ ኢዴፓ ከኅዳር 18 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ የድርድሩ አካል እንዳልሆነ እንገልጻለን፤›› በማለት ለፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድር መድረክ ደብዳቤ ጽፏል፡፡
የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ጫኔ ከበደ (ዶ/ር) ለሪፖርተር በጻፉት የኢሜይል መልዕክት፣ በአቶ አዳነ ፊርማ የወጣውን ደብዳቤ የኢዴፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ አያውቀውም ብለዋል፡፡ አቶ አዳነ የፓርቲው ሕጋዊ ፕሬዚዳንት ለመሆናቸው የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊያረጋግጥ እንደማይችልም አክለዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ የምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችን ለማግኘትና ሐሳባቸውን ለማካተት የተደረገው ጥረት ሊሳካ አልቻለም፡፡