ከአዲስ አበባ ሰሜን ምሥራቅ አቅጣጫ፣ ደብረ ብርሃን ከተማን አልፎ 170ኛ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው መልክአ ምድር፣ የአልፎ ሂያጁን ብቻ ሳይሆን ሥራዬ ብለው የሚመጡትን ጎብኚዎች (ቱሪስቶች) ቀልብ ይገዛል፡፡ ‹‹ገማሳ ገደል›› ይባላል፡፡ በሌላ በኩል 19ኛውና የ20ኛው ምዕት መጀመሪያ ላይ ነግሠው የነበሩት ዳግማዊ ምኒልክ አካባቢውን ያዘወትሩት ስለነበረ ‹‹የምኒልክ መስኮት›› እያሉም ይጠሩታል፡፡
ከደብረብርሃን ከተማ ሰሜን አቅጣጫ ከ4ዐ ኪሎ ሜትር በኋላ የሚገኘው ተፈጥሯዊ ስፍራ ጥድና ጅብ ዋሻ የሚባሉ አካባቢዎች ያዋሱኑታል፡፡ ከፍተኛ ተራራ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ከዓመት ዓመት ልምላሜ አያጣውም፡፡
በሰሜን ሸዋ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ድርሳን ላይ እንደተጻፈው፣ ከገማሳ ገደል ተፈጥሮአዊ ውበቱ ጋር ተዳምሮ በአካባቢው ያለው እንደ ጭስ የሚትጎለጎለው ጧት ከማታ ከስፍራው የማይለየው ጉምና ነፋሻማ አየር ባለቤት በመሆኑ ሁልጊዜ የማይሰለችና አስደሳች ስፍራ ያደርገዋል፡፡
‹‹ስፍራው ሆን ተብሎ የታቀደና በተዋጣለት መሐንዲስ ተከርክመው የተሠሩ የሚመስሉት ግራና ቀኝ እንደምስል ቀጥ ብለው የሚገኙትን ተራሮች ከነ ግርማ ሞገሳቸው የሚያገኙት በዚህ ቀዳዳ ወደ ምሥራቅ ቁልቁል አሻግረው ሲመለከቱ ያላሰቡትንና ያልጠበቁትን ክስተት ይመለከታሉ፡፡››
የይፋት ቆላማ መንደሮች ኢትዮጵያን ለሁለት ከፍሎ የሚያልፈው ትልቁ ስምጥ ሸለቆ የአፋር ክልል በረሃማ ቦታዎችና የአዋሽ ወንዝ በሰልፍ ተኝተው በአግራሞት የሚመለከቱበት ነው፡፡
ዳግማዊ አፄ ምኒልክ በንግሥና ዘመናቸው ወደ አያታቸው ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ የትውልድ ቦታ ወደሆነችው ሰላድንጋይ ከተማ ለተለያዩ ጉዳዮች ሲሄዱና ሲመለሱ በዚህ ስፍራ በመገኘት ትልቁ የስምጥ ሸለቆ የሚያልፍባቸውን አካባቢዎችና የአዋሽን ወንዝ በተመለከቱ ጊዜ እጅግ ከመደነቃቸው የተነሣ፣ በተደጋጋሚ በቦታው እየተገኙ ይመለከቱ ስለነበር፣ የአካባቢው ነዋሪዎችም የዚህን ስፍራ መጠሪያ ስም ‹‹የምኒልክ መስኮት›› የሚል ስያሜ ሰጥተውት እስካሁን ድረስ በዚሁ ስያሜ እየተጠራ መገኘቱን ድርሳኑ ያወሳል፡፡
ሥፍራው አምስቱን ወረዳዎችን ጣርማበርን፣ ባሶና ወራናን፣ አንኮበርን፣ መንዝ ማማ ምድርንና መንዝ ጌራን የሚያካልለው የወፍ ዋሻን ደን ከፊል ገጽታ ከስሩ የያዘ፣ ሁል ጊዜ ለምለም የማይለየው በመሆኑ በርካታ ዝንጀሮዎች፣ ሽኮኮዎችና ገደሉን እንደመጠለያ አድርገው የሚኖሩ በርካታ የአዕዋፍ ዝርያዎች የሚገኙበት መሆኑ ደግሞ የቱሪስት መስህብነቱን ማራኪ ያደርገዋል፡፡