ከሁለት ማከፋፈያዎች የኤሌክትሪክ ኃይል የምታገኘው የበርካታ ኢንዱስትሪዎች መናኸሪያ ሞጆ ከተማ አንደኛው ማከፋፈያ በገጠመው ብልሽት ምክንያት ከየካቲት 11 እስከ 13 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ በከፊል ጨለማ ውስጥ የቆየች ቢሆንም፣ መስመሩ ተስተካክሎ ሙሉ የኤሌክትሪክ ኃይል ማግኘቷ ተገለጸ፡፡
የኢንዱስትሪ ከተማ የሆነችው ሞጆ ከቆቃ ኃይል ማመንጫ ዘጠኝ ሜጋ ዋትና ስድስት ሜጋ ዋት ከሁለት ማከፋፈያዎች የኤሌክትሪክ ኃይል የምታገኝ ቢሆንም፣ ስድስት ሜጋ ዋት የሚያስተላልፈው ማሠራጫ ጣቢያ ብሬከር ተበላሽቶ ኃይል ተቋርጦ እንደነበር፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አገልግሎት ዲስትሪቢዩሽን ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ብርሃኔ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
የኃይል አገልግሎት አቅርቦቱ በመቋረጡ መከላከያ፣ ኬብል ማምረቻ ፋብሪካ፣ ኢትዮ ጃፓን ጨርቃ ጨርቅ፣ ሞጆ ዘይት ፋብሪካ፣ ሞጆ ቆዳ ፋብሪካ፣ ሸዋ ታነሪ (ኢስት አፍሪካ ታነሪ ተብሏል)፣ ሞጆ ደረቅ ወደብ፣ ነዋሪዎች በከፊልና የተለያዩ ድርጅቶች ለሦስት ቀናት ችግር እንደገጠማቸው ተናግረዋል፡፡
ከቆቃ ቃይል ማመንጫ 45 ኪሎ ቮልት ያገኝ የነበረውና ስድስት ሜጋ ዋት የሚያስተላልፈው ጣቢያ ብሬከር በመበላሸቱ የተቋረጠውን ኃይል ለመመለስ የአቃቂ፣ የአዋሽ ሰባትና አዲስ አበባ ዲስትሪክቶች ተረባርበው እንደሠሩ አቶ መስፍን አስረድተዋል፡፡
በመሆኑም ሞጆ ከተማ ከየካቲት 13 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ኃይል እያገኘች መሆኗን ገልጸው፣ የኢንዱስትሪዎቹ ባለቤቶችም ሆኑ ነዋሪዎች ላሳዩት ትብብርና ትዕግሥት ምሥጋናቸውን አቅርበዋል፡፡