ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የሽብር ተግባር ወንጀል ፈጽመዋል በማለት ክስ መሥርቶባቸውና እንደ ክሱ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል ተብሎ የስድስት ዓመታት ከስድስት ወራት ጽኑ ቅጣት ተወስኖባቸው የነበሩት የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ፣ የተቀጡበት አንቀጽ ተቀይሮ ቅጣታቸው በሦስት ዓመት ዝቅ አለ፡፡
የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ በሥር ፍርድ ቤት ማለትም የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አራተኛ ወንጀል ችሎት፣ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 6(3፣ 4 እና 6)ን መተላለፋቸውን ዓቃቤ ሕግ እንደ ክሱ በማስረጃ ማረጋገጡን ተናግሮ የሰጠውን ውሳኔ የቀየረው፣ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ነው፡፡
ችሎቱ በውሳኔው እንዳብራራው፣ የሥር ፍርድ ቤት በአቶ ዮናታን ላይ የስድስት ዓመት ከስድስት ወራት ጽኑ እስራት የቅጣት ውሳኔውን ያስተላለፈው፣ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ተከሳሹ የሽብር ተግባር ወንጀል ስለመፈጸማቸው የሚያረጋግጥ ማስረጃ ወይም ከሽብር ተግባር ጋር የሚያገናኝ ነገር ሳይኖር ነው፡፡ በመሆኑም አቶ ዮናታን ሊከሰሱና ጥፋተኛ ሊባሉ የሚችሉት በወንጀል ሕግ አንቀጽ 257(ሀ) መሠረት ማለትም፣ ‹‹በንግግር፣ በሥዕል ወይም በጽሑፍ አማካይነት በግልጽ የቀሰቀሰ፤›› በሚለው መሆን እንዳለበት በውሳኔው አስታውቋል፡፡
በመሆኑም አቶ ዮናታን ሊቀጡ የሚገባው የሥር ፍርድ ቤት እንደወሰነው ስድስት ዓመታት ከስድስት ወራት ሳይሆን፣ ሦስት ዓመታት ከስድስት ወራት መሆኑን በውሳኔው አስታውቋል፡፡ አቶ ዮናታን አንድ ዓመት ከ11 ወራት በእስር ላይ መቆየታቸው ታውቋል፡፡
አቶ ዮናታን በ2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ተከስቶ የነበረውን ብጥብጥ የሚያባብስ መጣጥፍ በኢሜይል አድራሻቸውና በድረ ገጽ በማሠራጨት፣ ሕዝቡን በማነሳሳት የሽብር ተግባር ወንጀል ፈጽመዋል የሚል ክስ እንደ ተመሠረተባቸውና የቅጣት ውሳኔ እንደተጣለባቸው መዘገባችን ይታወሳል፡፡