የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ላቀዳቸው ከፀሐይ ኃይል ለማመንጨት ባወጣው ዓለም አቀፍ ግልጽ ጨረታ፣ ከ60 በላይ ኩባንያዎች እየተፎካከሩ መሆናቸው ታወቀ፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ጨረታውን ያወጣው ባለፈው ዓመት አጋማሽ ሲሆን፣ ከፀሐይ ኃይል ለማመንጨት ያቀደባቸው አካባቢዎች ትግራይ፣ አማራ፣ አፋርና ድሬዳዋ ናቸው፡፡
የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፓነሎቹን በራሳቸው ገንዘብ ተክለው ኃይል እያመነጩ ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መሸጥ ዋነኛው የጨረታው መሥፈርት ሲሆን፣ በዚህ መሠረት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን 5,200 ሜጋ ዋት ኃይል ከፀሐይ ማመንጨት ይፈልጋል፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑት ኩባንያዎች በአራቱም የተገለጹ ሥፍራዎች የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክቶች ላይ ለመሳተፍ አስፈላጊውን ፋይናንስ ከራሳቸው ሒሳብ አዘጋጅተው መምጣታቸውን፣ በርካቶቹ ደግሞ ከአበዳሪዎች ጋር የገቡትን ስምምነት ይዘው መገኘታቸውን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡
በትግራይ ክልል ለታቀዱት ሁለት የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክቶች ከተሳተፉ ከ60 በላይ ኩባንያዎች ውስጥ፣ 18 የሚሆኑት ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፋቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ቀጣዩ ዙር ባቀረቡት ፋይናንስና ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያመረቱትን ኃይል በሚሸጡበት ታሪፍ ላይ የሚደረግ መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከእነዚህ አሥር ኩባንያዎች ውስጥ የጣሊያኑ ኢነርጂ ሪሶርስስ፣ ኢኒል ግሪን ፓወር፣ አሲዎና፣ ቲባኢኤ፣ ሰንኦሲስ የተባሉት በግዙፍነታቸው የሚታወቁ ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከፀሐይ ለማምረት ካቀደው የኤሌክትሪክ ኃይል በተጨማሪ 500 ሜጋ ዋት በጂኦተርማል፣ 420 ሜጋ ዋት ከባዮማስ፣ 5,200 ሜጋ ዋት ከንፋስ፣ እንዲሁም 7,500 ሜጋ ዋት ከውኃ ለማመንጨት በሁለተኛው የአምስት ዓመት መርሐ ግብር ዕቅድ ይዟል፡፡