‹‹ካሳ እንዲከፈለን እፈልጋለሁ። ታንዛንያ ሌሎች ጥቂት የአፍሪካ አገሮች በቅኝ አገዛዝ ዘመን ለተፈፀመባቸው በደል ከቀድሞዎቹ ቅኝ ገዢዎች ካሳ እንዲከፈላቸው በይፋ የጠየቁበትን አገባብ በአርአያነት ትከተላለች።››
የታንዛንያ የመከላከያና ብሔራዊ አገልግሎት ሚኒስትር ዶ/ር ሁሴን ምዌይኒ ከዶይቸ ቬለ ጋር ባካሄዱት ቃለ ምልልስ የተናገሩት፡፡
የታንዛንያ ፓርላማ ከምታመት በፊት ከ1905 እስከ 1907 በተካሄደው የነፃነት ተጋድሎ በማጂ ማጂ ነገድ አመፅ ላይ ጀርመን ለፈጸመችው ፍጅት፣ ካሳ እንድትከፍል መንግሥት ግፊት እንዲደርግ የካቲት 2 ቀን 2009 ዓ.ም. ማሳሰቡን ተከትሎ ነው ሚኒስትሩ ዶ/ር ሁሴን፣ በጀርመን ቅን አገዛዝ ዘመን የተፈፀመው በደል ሰለባ ለሆኑ በርካታ ግለሰቦች ቤተሰቦች ካሳ ሊከፈላቸው ይገባል በሚል ፓርላማው ያነሳውን ጥያቄ መንግሥት የመከታተልና የመጠየቅ ግዴታ እንዳለበት አስምረውበታል፡፡ አያይዘውም የክፍያው ተቋዳሽ የሚሆኑት የሰለባዎቹ ተወላጆች እንጂ የመንግሥት ካዝና አይሆንም ብለዋል፡፡ ታሪካዊ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ ከ1880ዎቹ መጨረሻ እስከ 1919 በወቅቱ ‹‹ታንጋኒካ›› ትባል በነበረችው ያሁኗ ታንዛኒያ በ‹‹የጀርመን ምሥራቅ አፍሪካ›› አገዛዝ ላይ ዓመፅ ባነሱት የማጂ ማጂ ጎሳ አባላት ላይ በተሰነዘረ ጥቃት 10,000 ሰዎች ተገድለዋል፣ ተሰቃይተዋል፡፡ በበርሊን ሙዚየሞች ውስጥ ከቀድሞ ‹‹የጀርመን ምሥራቅ አፍሪካ›› (ታንዛኒያና ሩዋንዳ) የመጡ በመቶ የሚቆጠሩ አንገታቸው የተቀላ አፍሪካውያን የራስ ቅሎች መኖራቸውን በቅርቡ መጋለጡን የዶይቸ ቬለ ዘገባ አስታውሷል፡፡