ከነበሩበት ቀዬና ይዞታቸው የሚፈናቀሉ የኅብረተሰብ ክፍሎች ሲስተናገዱ የቆዩበት የካሳና ምትክ ቦታ አዋጅ ቁጥር 455/1997 ሊሻሻል ነው፡፡ በዚህ አዋጅ ሲስተናገዱ የቆዩ የከተማና የገጠር ነዋሪዎች የካሳና የምትክ ቦታ ቀመር አነስተኛ በመሆኑ፣ ለከፍተኛ ጉዳት እየተዳረጉ መሆኑን ሲገልጹ የቆዩ ስለሆኑና መንግሥት ዘግይቶም ቢሆን ቅሬታውን በመስማት አዋጁ እንዲሻሻል ወስኗል፡፡
ይህንን አዋጅ የማውጣት ሥልጣን ያለው የፌዴራል የተቀናጀ መሠረተ ልማቶች ማስተባበሪያ ኤጀንሲ ሲሆን፣ ኤጀንሲው ከከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር እንዲሁም ከእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ሚኒስቴር ጋር በጋራ እየሠራ መሆኑ ታውቋል፡፡
በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተሞችና በዘጠኙም ክልሎች በርካታ ፕሮጀክቶች በመካሄድ ላይ ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ ፕሮጀክቶች መካከል የባቡር መስመር፣ የመንገድ አውታር፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ፣ የቴሌኮም፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ የቤቶች ልማትና የግል ባለሀብቶች የሚያካሂዳቸው ፕሮጀክቶች ተጠቃሾች ናቸው፡፡
እነዚህን ፕሮጀክቶች ለማካሄድ በርካታ የከተማ ነዋሪዎች፣ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ከነበሩበት ቀዬ ሲፈናቀሉ ቆይተዋል፡፡
ነገር ግን ከነበሩበት ቀዬ የሚፈናቀሉት እነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎች፣ የሚሰጣቸው ምትክ ቦታና ለንብረታቸው የሚሰጣቸው ክፍያ አነስተኛ መሆኑ ቅሬታ ፈጥሮባቸው ቆይቷል፡፡
በዚህ ምክንያት ተፈናቃዮች ለተለያዩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች ከመዳረጋቸውም በላይ፣ የዕለት ተዕለት ኑሮአቸውን ለመግፋት እንኳ እየተቸገሩ መሆኑን በተለያዩ መድረኮች ሲያነሱ ነበር፡፡
ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የመሬት ሥሪት ባለሙያዎችም እንደሚሉት፣ የካሳና የምትክ ቦታ አሰጣጥ የሚያስፈጽም ተቋም ባለመኖሩ በተለያዩ አካባቢዎች የተለያዩ የካሳ ክፍያ ሥርዓቶች እንዲኖር አድርጓል፡፡ የግምት ሥራው በኮሚቴ የሚሠራ በመሆኑ ለሙስና በር እየከፈተ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ለልማት ተነሺዎች የካሳ ክፍያ ሲፈጸም ተነሺዎቹ የተሻለ ኑሮ እንዲኖሩ ወይም ከነበሩበት የኑሮ ደረጃ እንዳይወርዱ በማሰብ ቢሆንም፣ ባለፉት ዓመታት ግን ይህ ፍላጎት በፍፁም ተግባራዊ እንዳልተደረገ ገልጸዋል፡፡
የፌዴራል የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ማዕከል ባካሄደው ጥናት የልማት ተነሺ አርሶ አደሮች በዘላቂነት እንዲቋቋሙ የሚያስችል የማቋቋሚያ ፓኬጅ ባለመኖሩ ምክንያት፣ ከልማቱ ተጠቃሚ ከመሆን ይልቅ ተጎጂ እየሆኑ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡ ተነሺዎችን ማቋቋም ተገቢውን ትኩረት አግኝቶ ፓኬጅ ተቀርፆለት የግድ መከናወን ያለበት ዋና ሥራ ስለሆነ፣ የፖሊሲ አቅጣጫ ሊቀመጥለትና አርሶ አደሮችም፣ አርብቶ አደሮችም የሚቋቋሙበት ስትራቴጂ ሊኖር እንደሚገባ አመልክቷል፡፡
ማዕከሉ በልማት ምክንያት ከቀያቸው የሚነሱ የኅብረተሰብ ክፍሎች ሊደረግላቸው ስለሚገቡ ጉዳዮች ለመምከር፣ በዚህ ሳምንት መጨረሻ የውይይት መድረክ ማዘጋጀቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡