የትራፊክ አደጋ በአገራችን በቀን ከሰባት ሰዎች በላይ ለጉዳት ይዳርጋል፡፡ እግረኞች ዘንድ የጥንቃቄ ንዝህላልነት ቢኖርም ከ85 በመቶ በላይ የጉዳቱ ተጠቂዎች ሾፌሮች ናቸው፡፡ የክህሎት፣ የሥነ ምግባር፣ የመንገድ ደኅንነት፣ አደጋን ቀንሶ የማሽከርከር ጉድለት መኖሩና የመንጃ ፈቃድ አሰጣጡ ከሙስና የፀዳና ደረጃውን የጠበቀ አለመሆኑ ለሚከሰቱ የትራፊክ አደጋዎች እንደምክንያት ይጠቀሳሉ፡፡
የሾፌሮች ሙያውን አክብረው ማሽከርከር ችግሩን ለመቅረፍ አንዱ መንገድ ሲሆን፣ ሙያን የሚያከብሩ ሾፌሮችን ለማበረታታትና ዕውቅና ለመስጠትም፣ ‹‹ክብር ለሾፌሮች›› በሚል መሪ ቃል ዓለም አቀፍ የሾፌሮች ቀን በኢትዮጵያ ጥር 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ተከብሯል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መንገዶች ባለሥልጣንና የሾፌሮች ማኅበር አዘጋጅነት በተከናወነው በዚሁ በዓል ላይ፣ አሥር ምስጉን ሾፌሮች ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መንገድና ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ኢንጂነር ሰለሞን ኪዳኔ የዕውቅና ሠርተፍኬት ተቀብለዋል፡፡
የሾፌሮች ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘውዱ ለማ፣ ለኅብረተሰቡ አገልግሎት የሚሰጡ አሽከርካሪዎች እንዲከበሩ፣ በቅድሚያ ኅብረተሰቡን ማክበር እንዲሁም ለሕግና ለሕልውና መገዛት የሚያስፈልግ ቢሆንም፣ ብዙ ጊዜ የሚታየው ከዚህ የተቃረነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ትራፊክ ፖሊሲና ሾፌር አባራሪና ተባራሪ ሆነው እንደሚታዩ፣ በዚህ ዓይነቱም ድብብቆሽ የሚደርሰው ጉዳት ብዙ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መንገድና ትራንስፖርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ቢኒያም ምክሩ፣ የሾፌሮችን ብቃት ከማረጋገጥ ጋር በተገናኘ እየተሠራበት ያለው አካሄድ፣ አንድ የመንጃ ፈቃድ የሚያወጣ ሰው በአግባቡ ልምድን እያካበተ ወደ ላይ የሚወጣበት ባለመሆኑ ክፍተት መኖሩን ጠቁመዋል፡፡
ይህን ችግር ለመቅረፍ የሚያስችል መመሪያ እንደተረቀቀ፣ በቅርቡ ጸድቆ ወደ ሥራ እንደሚገባ፣ ከብቃት ማረጋገጫና ከመንጃ ፈቃድ አሰጣጥ ጋር የተገናኙ ችግሮችንም ለመቅረፍ በቅድሚያ የመዋቅር ማስተካከያ ለማድረግ እንደተሞከረም አክለዋል፡፡
ችግር ለነበረባቸው ማሠልጠኛ ተቋማት ማስጠንቀቂያ ከመስጠት እስከ መዝጋት ዕርምጃ መወሰዱንና መንጃ ፈቃድ የሚያወጣ ሰው አዲስ አበባ ውስጥ በተመረጡ ቦታዎች ላይ የተወሰነ ሰዓት ተለማምዶ ወደ ፈተና እንዲመጣ ለማድረግ የሚያስችል ሥራ መጀመሩንም አስታውሰዋል፡፡
ለትራፊክ አደጋ መንስዔ ከሆኑት የመንገድ አለመመቻቸት አንዱ ሲሆን፣ መሀልና ቀለበት እንዲሁም ብዙ የትራፊክ ፍሰት ያሉባቸው መንገዶች ከክረምት ጋር በተያያዘ በሚገጥማቸው ጉዳት ለአደጋዎችና ለግጭቶች መንስዔ በመሆናቸው፣ ባለፉት አራት ወራት ጥገና መከናወኑን የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ ተናግረዋል፡፡