ከ1975 ዓ.ም. ጀምሮ የስፖርት ማኅበር በማቋቋም ላለፉት 34 ዓመታት በስፖርት ውስጥ ሲወዳደር የቆየው የኢትዮጵያ መድን ድርጅት (ኢመድ)፣ ሁለገብ የስፖርት ማዘውተሪያ ማዕከል ሊያስገነባ መሆኑን አስታወቀ፡፡ ድርጅቱ ማክሰኞ ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. ለግንባታው የሚያስችለውን የመሠረት ድንጋይ አኑሯል፡፡
ኢመድ ለሪፖርተር በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው ከሆነ፣ ቃሊቲ ከክራውን ሆቴል ጀርባ የሚገኘውን የስፖርት ማኅበሩ ማዘውተሪያ የነበረውን በማሻሻል፣ ደረጃውን የጠበቀ የስፖርት ማዕከል ለመገንባት የሚያስችለውን ዝግጅት አጠናቋል፡፡ በመግለጫው መሠረትም ከሁለት ፎቅ የሕንፃ ግንባታ ባሻገር ከ40 የማያንሱ የመኝታ ክፍሎች፣ በቂ የመታጠቢያና የመመገቢያ ክፍሎች፣ የራሱ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማዘውተሪያ (ጂም) እንደሚያካትትም ተገልጿል፡፡ ለግንባታው ከ15 እስክ 20 ሚሊዮን ብር በጀት መያዙም ተገልጿል፡፡
የመድን እግር ኳስ ክለብ ለበርካታ ዓመታት በፕሪሚየር ሊግ የተሳተፈ ከመሆኑ ባሻገር፣ በ1985 እና 1986 ዓ.ም. ኢትዮጵያን በመወከል በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ እስከ ሩብ ፍጻሜ መግባት የቻለ ነው፡፡ ክለቡ በአሁኑ ወቅት ምንም እንኳ በአገሪቱ ከፍተኛ ሊግ እየተሳተፈ ቢሆንም፣ ቀደም ባሉት ዓመታት ግን ለኢትዮጵያ ዋናውና ወጣት ቡድን በርካታ ተጨዋቾችን በማፍራት የሚታወቅ ክለብ መሆኑ አይዘነጋም፡፡