ከ200 በላይ ታዋቂ ሴት አትሌቶች የሚሳተፉበት የአምስት ኪሎ ሜትር ታላቁ የሴቶች ብቻ የጎዳና ላይ ሩጫ 11,000 ተሳታፊዎች እንደሚያወዳድር ተገለጸ፡፡
ይኸው ለ13 ዓመታት ሲካሄድ የቆየው የሩጫ ውድድር የኢትዮጵያ ሴቶችን ስኬት ለመዘከርና ዕውቅና ለመስጠት ታስቦ መጋቢት 3 ቀን 2009 ዓ.ም. እንደሚካሄድ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዝግጅት ክፍል አስታውቋል፡፡
‹‹ቅድሚያ ለሴቶች›› (UN 2017 WOMEN FIRST 5 KM) በሚል መሪ ቃል የሚካሄደውን ውድድር ተወዳዳሪዎች ርቀቱን ከ35 ደቂቃ በታች በመግባት ሩጫውን እንዲጨርሱ ለማድረግ መታሰቡን ጭምር ዝግጅት ክፍሉ አስታውቋል፡፡ የኦሊምፒክና የዓለም ሻምፒዮኗና የሴቶች ውድድር በጎ ፈቃድ አምባሳደር መሠረት ደፋር ይህን ለማሳካት መነሳቷም ተጠቅሷል፡፡
ውድድሩ ‹‹ስለምትችል›› የሚል መሪ ቃል ያለው መሆኑን ያስታወቀው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ፣ ከተባበሩት መንግሥታት 17ቱ የዘላቂ ልማት ግቦች ውስጥ የፆታ እኩልነት ጉዳይን ትኩረት በማድረግና ከፆታ ጋር የተገናኙ ጥቃቶችን ለማስቆም እንዲሁም ሴቶችን ወደ አመራር ለማምጣት ህልምን ከግብ ለማድረስ እየሠራ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡
ከአንድ ወር በኋላ ለሚካሄደው ውድድር ምዝገባው የካቲት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. በይፋ ይጀመራል፡፡ ለዚህ ተብሎ አምስት የምዝገባ ጣቢያዎች ማለትም፣ በእናት ባንክ አራት ቅርንጫፎች በመገናኛ አበበች ጎበና ቅርንጫፍ፣ በካሳንቺስ እቴጌ ጣይቱ ቅርንጫፍ፣ በሜክሲኮ ደራርቱ ቱሉ ቅርንጫፍና በአዲሱ ገበያ ሜሪ አርምዴ ቅርንጫፍ እንዲሁም በአምስተኛው በካፒታል ሆቴልና ስፓ መሆኑን ጭምር አስታውቋል፡፡
ተምሳሌት ሴቶች ጨምሮ ከ11,000 በላይ ሴቶችን ብቻ ሲያሳትፍ የቆየው ውድድር በአሁኑ ወቅት ለዓለም አቀፍ ዕውቅና ከበቁ አትሌቶች መካከል አሰለፈች መርጊያና ሰንበቴ ተፈሪ የተገኙበት ነው፡፡ በቅድሚያ ለሴቶች 5 ኪሎ ሜትር ውድድር ላይ አሰለፈች 15፡57 ደቂቃ በርቀቱ ሲኖራት፣ ሰንበሬ ተፈሪ ደግሞ 15፡55 ያስመዘገበችው ምርጥ ሰዓቷ እንደሆነም ተመልክቷል፡፡