በለንደን የ2012 ኦሊምፒክ በ3,000 ሜትር መሠናክል ያገኘችው የነሐስ ሜዳሊያ በአምስተኛ ዓመቱ ወደ ብር ሜዳሊያ የተቀየረላት ሶፊያ አሰፋ ክብሩን ሐሙስ ጥር 25 ቀን 2009 ዓ.ም. ተቀበለች፡፡
በ30ኛው ኦሊምፒያድ በርቀቱ አንደኛ ወጥታ የነበረችው ሩሲያዊቷ ዩሊያ ዛራፖቫ አበረታች ንጥረ ነገር (ዶፒንግ) መውሰዷ በመረጋገጡና እንድትሰርዝ በመደረጉ በተደረገው ሽግሽግ ሦስተኛ የወጣችው ሶፊያ ወደ ሁለተኛ፣ ሁለተኛ የነበረችው ቱኒዝያዊቷ ሀቢባ ግሪቢ ወደ አንደኛ፣ አራተኛ የወጣችው ኬንያዊቷ ሚልካ ቼሞዝ ወደ ሦስተኛ እንዲያድጉ ተደርጓል፡፡ ሌሎቹ ኢትዮጵያውያት ሕይወት አያሌውና እቴነሽ ዲሮ ደረጃቸው ወደ አራተኛና አምስተኛ ከፍ ብሏል፡፡
በኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴ ውሳኔ መሠረት ኦሊምፒያን ሶፊያ አሰፋ በድሪምላይነር ሆቴል በተደረገው ሥነ ሥርዓት ከኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴ አባልና የዓለም ባድሜንተን ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ዳግማዊት ግርማይ ብርሃኔ እጅ የብር ሜዳሊውን ተቀብላለች፡፡
‹‹የብር ሜዳሊያውን ያገኘሁት በወቅቱ ቢሆን ኖሮ ደስታዬ እጥፍ ድርብ ይሆን ነበር፤›› በማለት የተናገረችው ሶፊያ፣ ከጥቅማ ጥቅም አንፃር በመግቢያና በኮንትራት በብዙ ነገሮች መጠቀም ያስችላት እንደነበር አልሸሸገችም፡፡ ‹‹አራት ዓመት ቆይቶም ቢሆን ጊዜውን ጠብቆ መጥቷልና ደስተኛ ነኝ፤›› ሳትልም አላለፈችም፡፡ እግረ መንገዷንም አትሌቶች ከዶፒንግ መራቅ እንዳለባቸውም መልዕክቷን ስታስተላልፍ ‹‹ዶፒንግ ተጠቅሞ መሮጥና ጊዜያዊ ደስታ ማግኘት ምንም ዓይነት ሰላም አይሰጥም፤›› ነበር ያለችው፡፡
በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ ከ37 ዓመት በፊት በተካሄደው የሞስኮ ኦሊምፒክ፣ በኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ታሪክ በ3,000ሜትር መሠናክል የነሐስ ሜዳሊያ፣ ቀደም ብሎም በዓለም አትሌቲክስ ዋንጫ ለአፍሪካ ብር ሜዳሊያ ያስገኘው ሻምበል እሸቱ ቱራን ጨምሮ፣ የብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ሥራ አስፈጻሚ ቦርድ አባላት፣ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ፣ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
በለንደን ኦሊምፒክ በወቅቱ የነበረው የኢትዮጵያ ደረጃ ከ24ኛ ወደ 22ኛ በተሸጋገረበት መድረክ ላይ ሦስት ወርቅ፣ አንድ ብርና ሁለት ነሐስ ያስገኙት አትሌቶች አልታዩም፡፡
ቱኒዚያዊቷ ሀቢባ ግሪቢ የሩሲያዊቷን የለንደን ኦሊምፒክና የዴጉ ዓለም ሻምፒዮና ሁለት ወርቆች፣ በቱኒስ አቅራቢያ በምትገኘው ሬዴስ ከተማ የተሸለመችው፣ ከስምንት ወራት በፊት (ግንቦት 27 ቀን 2008 ዓ.ም.) ነበር፡፡ ከ23 ዓመት በታች የሜዲትራኒያን ጨዋታዎች ላይ በተዘጋጀ ልዩ ሥነ ሥርዓት ወርቆቹን ያጠለቁላት ሞሮኳዊቷ የኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴ ምክትል ፕሬዚዳንት ናዋል ኢል ሙታውኬል ናቸው፡፡