ክልሎችና ትልልቅ የከተማ አስተዳደሮች የመሬት አቅርቦት ላይ የሚሠሩ ኮርፖሬሽኖችን ሊያቋቁሙ ነው፡፡ የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር ኮርፖሬሽኖችን ማቋቋም የሚያስችል ሞዴል ደንብ አዘጋጅቶ አስተያየት እንዲሰጥበት እያደረገ ነው፡፡
የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር የ2009 ዓ.ም. የመጀመርያ ግማሽ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት እንደሚያስረዳው፣ የከተሞች የመሬት አቅርቦት እንዲሻሻል የመሬት አቅርቦት ኮርፖሬሽን እንዲያቋቁሙ ይደረጋል፡፡
የሚቋቋመው ኮርፖሬሽን አደረጃጀት ምን መምሰል እንዳበት በአማካሪ ኩባንያ ለማስጠናት ጨረታው ሒደት ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡
የመሬት ዝግጅት በተለይ በከተሞች ከፍተኛ ችግር እየሆነ በመምጣቱ ራሱን የቻለ ሥልጣን ባለው አካል ማሠራት አስፈላጊ መሆኑ እንደታመነበት ተገልጿል፡፡
በዚህ መሠረት አዲስ አበባና ድሬዳዋ እንዲሁም ሌሎች ትልልቅ ከተሞች በመሬት አቅርቦት ላይ የሚሠሩ ኮርፖሬሽኖችን እንደሚያቋቁሙ ይጠበቃል፡፡
ኮርፖሬሽኖቹ የመሬት ዝግጅት ሥራዎችን በዋናነት ሸንሽኖ ወሰን ማስከበርና መሠረተ ልማት ዝርጋታ ያከናውናሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ካሳ ክፍያ፣ ለተነሽዎች ምትክ ቤትና ቦታ አቅርቦት፣ የለማ መሬት በጨረታና በምደባ ማስተላለፍ፣ የሊዝ ክፍያና አፈጻጸም ሥራዎችን ያከናውናሉ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቅድሚያ ወስዶ የመሬት ልማት ኮርፖሬሽን ማቋቋም የሚያስችለውን እንቅስቃሴ ጀምሯል፡፡
በአዲስ አበባ መሬት ላይ ሥልጣን ያለው የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ነው፡፡ ይኼ ቢሮ በሥሩ ባሉ ስድስት ኤጀንሲዎች አማካይነት የክትትልና ግምገማ፣ እንዲሁም የመሬት ልማትና አቅርቦት ሥራዎች ላይ ሲሠራ ቆይቷል፡፡ ነገር ግን ከጥቂት ጊዜያት ወዲህ መሻሻል እያሳየ ቢሆንም፣ በመሬት አቅርቦት በኩል በዕቅዱና በአፈጻጸሙ መካከል ሰፊ ክፍተት መኖሩን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
በቀረበው ሪፖርት ላይ እንደተመለከተው በተያዘው በጀት ዓመት በተወሰኑ ከተሞች 25,000 ሔክታር መሬት ለተለያዩ አገልግሎቶች ለማቅረብ ታቅዶ ነበር፡፡ ነገር ግን በስድስት ወራት መዘጋጀት የቻለው 3,238.11 ሔክታር ብቻ ነው፡፡ ይኼንን ደካማ የሥራ አፈጻጸም አዳዲሶቹ ኮርፖሬሽኖች ይለውጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡