ባለፉት ስድስት ወራት የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ የወጪ ንግድ ገቢ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ማሽቆልቆሉ ተገለጸ፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ማክሰኞ ጥር 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት፣ ከማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ይገኛል ተብሎ ከሚጠበቀው 349 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ ሊገኝ የቻለው 198.5 ሚሊዮን ዶላር መሆኑን ገልጿል፡፡ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ አብተው ባቀረቡት ሪፖርት እንደገለጹት የስድስት ወራቱ የገቢ አፈጻጸም 56.5 በመቶ ብቻ ነው፡፡
ከጨርቃ ጨርቅ ዘርፍ ይገኛል ተብሎ ከታቀደው መገኘት የተቻለው 55.5 በመቶ ያህሉ ብቻ ሲሆን፣ ይኼም ካለፈው ዓመት በተመሳሳይ ወቅት በ0.5 በመቶ ቅናሽ ያሳየ መሆኑን፣ ከቆዳና የቆዳ ውጤቶች የገቢ ዕቅድ የተገኘው 50.4 በመቶ ካለፈው ዓመት 7.5 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱን ሚኒስትሩ አስረድተዋል፡፡
እንዲሁም ከሥጋ የወጪ ንግድ የገቢ ዕቅድ ሊገኝ የተቻለው 61.6 በመቶ ያህሉ ሲሆን፣ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ5.1 በመቶ ቅናሽ አሳይቷል ብለዋል፡፡
ሚኒስትሩ እንዳሉት፣ የወጪ ንግድ ገበያ መቀዛቀዝ በቆዳ ዘርፍ ለታየው የኤክስፖርት አፈጻጸም ጉድለት ተጠቃሽ ነው፡፡ በተመሳሳይ የጨርቃ ጨርቅ ዘርፉ በዓለም ገበያ መቀዛቀዝ ምክንያትና የተሻለ ትርፍ ፍለጋ የአገር ውስጥ ገበያ ላይ በማተኮሩ የገቢ አፈጻጸም ማሽቆልቆሉን ገልጸዋል፡፡
የምክር ቤቱ የኢንዱስትሪ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በሰጠው አስተያየት ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ኢንቨስተሮች ገበያ ተኮር እንዲሆኑ ማበረታታትና የበለጠ ምርት በመላክ የተገኘውን ገበያ መጠቀም እንዳለበት አሳስቧል፡፡