ዓለም በከፍተኛ ፍጥነት በመለወጥ ላይ ነው፡፡ በአገሮች መካከልና በተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት መካከል የነበሩት ግንኙነቶች ገጽታቸው እየተለወጠ ነው፡፡ አዳዲስ ክስተቶችም እየታዩ ነው፡፡ ለምሳሌ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በቀይ ባህር አካባቢ የሚታየው የዓረብ አገሮች እንቅስቃሴ፣ ግብፅ በጎረቤት አገሮች አካባቢ ገባ ወጣ ስትል መታየቷ፣ አንፃራዊ መረጋጋት እየታየበት የነበረው የአፍሪካ ቀንድ አካባቢ በዓረብ ባህረ ሰላጤ አገሮች ትኩረት ውስጥ መግባቱ፣ የአውሮፓ ኅብረትን ለማፍረስ የተነሳሱ የአውሮፓ አገሮች ፅንፈኛ የቀኝ ክንፍ ፓርቲ መሪዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ ድምፃቸው ጎልቶ መሰማቱ፣ አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ በአሜሪካ የመጨረሻውን ሥልጣን ጨብጠው አዳዲስ ዕርምጃዎችን መውሰድ መጀመራቸው፣ አሜሪካን ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አባልነት ለማስወጣት በሪፐብሊካን ፓርቲ የሕግ ረቂቅ መዘጋጀቱ፣ ወዘተ የዓለምን አዲስ የለውጥ ክስተት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ይህ ለውጥ አዎንታዊም ይሁን አሉታዊ እንደ አገር መዘጋጀት ግን የግድ ይሆናል፡፡
አጠቃላዩን የዓለም ተጨባጭ ሁኔታ ከአካባቢያችን አገሮች በመነሳት ስንቃኘው፣ ከዚህ በፊት ከፍተኛ መስዋዕትነት በተከፈለበት የአካባቢው ሰላምና መረጋጋት ላይ አደጋ የሚደቅኑ ሥጋቶች እየተሰሙ ነው፡፡ በሶማሊያ ያለው እዚህ ግባ የማይባል የፀጥታ ሁኔታ አሁንም ለአካባቢው አገሮች ከፍተኛ ሥጋት ነው፡፡ በቅርቡ እንደ አገር የተመሠረተችው ደቡብ ሱዳን ለአካባቢው ጠንቅ የሆነው የውስጥ ችግሯ አልበቃ ብሎ፣ የወደፊቷ ችግር ፈጣሪ መሆኗ ከአሁኑ ምልክቶች እየታዩ ነው፡፡ የደቡብ ሱዳን ውስጣዊ ችግርን ወደ ውጭ የመግፋት ፍላጎት ለኢትዮጵያ ችግር ፈጣሪ እንደሚሆን ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ በተለይ ግብፅ በአካባቢው የምታደርገው ማንዣበብ ብዙ የሚናገረው ነገር አለው፡፡ ሰሞኑን ማስተባበያ የተሰጠበት ነገር ግን በተለያዩ ሚዲያዎች ብዙ የተባለበት የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት የግብፅ ጉብኝትና አደረጉት የተባለው ስምምነት፣ እንደ ዋዛ የሚታለፍ ሳይሆን ጥልቅ የሆነ ፍተሻ የሚያስፈልገው ነው፡፡ ከሌሎች ጎረቤት አገሮች ጋር ያለው ግንኙነትና እነሱ ስለኢትዮጵያ ያላቸው ወቅታዊ ምልከታም እንዲሁ መፈተሽ አለበት፡፡ የዓለም አሠላለፍ ሲቀየር ነቃ ብሎ ማየት ለአገር ህልውና ይበጃል፡፡
ወደ አገራችን የውስጥ ጉዳይ ስንመለስ አገሪቱን ለዘመናት ከባዕዳን ቅኝ አገዛዝም ሆነ ወረራ መከላከል የተቻለው ሕዝቡ በአንድነት ሆኖ አገሩን በመጠበቁ ነው፡፡ በተለያዩ ዘመናት በጨቋኝና በአምባገነን ገዥዎች ከፍተኛ በደል እየደረሰበት እንኳ ከአገሩ አንዳችም ነገር ያላስቀመደው ይህ የተከበረ ሕዝብ፣ ለዓለም ጥቁር ሕዝቦች መመኪያ የሆነውን ታላቁን ፀረ ኮሎኒያኒስት ድል በዓደዋ ተራሮች ላይ ያስመዘገበው በጠንካራ አንድነቱና ኅብረቱ ብቻ ነው፡፡ መላው የአገራችን ሕዝብ ለአገሩ ከነበረው የጋራ ፍቅር የተነሳ ለአውሮፓ ቅኝ ገዥዎች ባለመንበርከክ አገሩን ከአፍሪካ ቀዳሚዋ አገር አድርጓታል፡፡ አገሩን በእንዲህ ዓይነቱ ወደር የሌለው ፍቅር ሲጠብቅ የኖረው ይህ ጀግና ሕዝብ፣ በውስጡ ያሉ ተፈጥሯዊ ልዩነቶች ሳይገድቡት ዘመናትን አብሮ ተሻግሯል፡፡ ይህንን ታላቅ ሕዝብ ይዞ ተዓምር መሥራት ሲቻል በማይረቡና እዚህ ግቡ በማይባሉ ልዩነቶች በመከፋፈል አገርን ለአደጋ ማጋለጥ በታሪክ ያስጠይቃል፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ የሁሉም ዜጎቿ የጋራ መኖሪያ እንድትሆን፣ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍንባትና ታፍራና ተከብራ ወደ ብልፅግና እንድታመራ ማንኛውም መስዕዋትነት መከፈል አለበት፡፡
ይህ መስዕዋትነት የሚጀምረው ከመንግሥት ነው፡፡ መንግሥት በተለይም ገዥው ፓርቲ ኢትዮጵያ የሁሉም ዜጎች የጋራ እናት መሆኗን የሚያረጋግጡ ሥር ነቀል ዕርምጃዎች ይጠበቁበታል፡፡ ከእነዚህም መካከል በአገሪቱ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ዕውን እንዲሆን የተዘጋጋውን የፖለቲካ ምኅዳር በአስቸኳይ መክፈት፣ ሰላማዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃነት የሚፎካከሩበት ምዕራፍ እንዲጀመር መደላደሉን ማመቻቸት፣ ዜጎች የሚፈልጉትን በነፃነት የሚመርጡበት የምርጫ ሥርዓት መፍጠር፣ የሕግ የበላይነት ተከብሮ ሁሉም ዜጋ በሕግ ፊት እኩል መሆኑ በተግባር እንዲረጋገጥ ማድረግ፣ ሕዝብ በፍፁም ሳይሸማቀቅ በአገሩ ጉዳይ ባለቤት መሆኑን የሚያምንበት ዓውድ መፍጠር፣ የመንግሥት አሠራር በግልጽነትና በተጠያቂነት መንገድ እየተከናወነ መሆኑን በተግባር ማሳየት፣ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ያሉ መገናኛ ብዙኃንን ለሁሉም ወገን እኩል ተደራሽ ማድረግ፣ ተጠያቂነትን በማጠናከር የሕዝብ ሀብትን ከዘረፋና ከብክነት ማዳን፣ እጅግ አስመራሪ የሆነውን ኢፍትሐዊነት በፍጥነት ማስወገድ፣ ወዘተ ጊዜ የማይሰጣቸው ዕርምጃዎች ናቸው፡፡ ሕዝብ በገዛ አገሩ ባለቤት መሆኑንና ፍትሐዊ ተጠቃሚ እንደሆነ አመኔታ የሚኖረው ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈኑበት ሥርዓት ሲገነባ ብቻ ነው፡፡ አሁን ሕዝብ አገሩን የሚወደውና ከጥቃት የሚጠብቀው ይህ ዓይነት ሥርዓት እንደሚገነባ መተማመኛ ሲያገኝ ነው፡፡ ጥቂቶች የሚከብሩበትና እንደፈለጉ የሚሆኑበት ሥርዓት ግን ለአገር ውስጥም ሆነ ለውጭ ጥቃት የተጋለጠ ነው፡፡ ይህ በቂ ግንዛቤ ሊያዝበት ይገባል፡፡ ሥልጣን ከአገር አይበልጥም፡፡ ከአገር በላይ ምንም የሚቀድም የለም፡፡
በተቃውሞ ጎራ የተሠለፉ ኃይሎችም ሆኑ ሌሎች ወገኖች አገርን ማስቀደም ኃላፊነታቸው ሊሆን ይገባል፡፡ ከገዥው ፓርቲም ሆነ ሥልጣን ላይ ካለው መንግሥት ጋር የሚያደርጉት ሰላማዊ ትግል እንዳለ ሆኖ፣ ከሥልጣን በፊት ለአገርና ለሕዝብ ዘለቄታዊ ሰላምና ብልፅግና ሲሉ ድርድርን ማስቀደም አለባቸው፡፡ ድርድር የሚጀመረው ከአሰልቺ ውይይትና ክርክር በኋላ መሆኑን ባለመገንዘብ፣ ቅድመ ሁኔታዎችን በመደርደርና ከዚህ በፊት የነበሩ ሰቆቃዎችን በማስታወስ ከአዙሪቱ ውስጥ ካልወጡ ማንም ተጠቃሚ አይሆንም፡፡ በእልህና በቂም የተሞላው የተበላሸ ግንኙነት ወደ ጎን ተገፍቶ የተጀመረው አዲስ ምዕራፍ ውጤታማ እንዲሆን በትዕግሥት ሊሠሩ ይገባል፡፡ የገዥው ፓርቲ አካሄድ አላምር ቢል እንኳ ተስፋ ባለመቁረጥ እስከ መጨረሻው ድረስ ሳይታክቱ አማራጮችን ይዘው መቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ በሳል ፖለቲከኛና ብልህ ነጋዴ በስተመጨረሻው ካሰቡት ሊደርሱ የሚችሉት ተደራዳሪዎቻቸውን በሚገባ ለማሳመን በመቻላቸው ነው፡፡ አስቸጋሪውን ጉዞ በውጤት ለማጀብ ብልኃት አስፈላጊ ነው፡፡ በየምዕራፉ በመበሳጨት ተስፋ መቁረጥ ለአገርም ሆነ ለሕዝብ የሚፈይደው የለም፡፡ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በጉልበት እንደማይገነባ ሁሉ፣ ሕዝብ የሚፈልገውን ሥርዓት ማምጣት የሚቻለው ደግሞ የሕዝብን አጀንዳ በማስቀደም ብቻ ነው፡፡ ለዚህም ሲባል ላብ ጠብ እስኪል መደራደር የግድ ይሆናል፡፡ የዓለምን ተጨባጭ ሁኔታ መገምገምም ተገቢ ነው፡፡ ለአገርና ለሕዝብ ዘለቄታዊ ህልውና ሲባል አስፈላጊው መስዕዋትነት ሁሉ ይከፈል፡፡ ሕዝብና አገርን ማስቀደም ያስከብራል፡፡
የዓለም የፖለቲካ አካሄድ ወትሮ ከሚታወቀው እያፈነገጠ ነው፡፡ አገሮች ከመቼውም ጊዜ በላይ ጥቅሞቻቸው ላይ ብቻ እያተኮሩ ነው፡፡ ‹‹አሜሪካን ወደ ታላቅነቷ መመለስ›› የሚለው የፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ፖሊሲ ‹‹አሜሪካ ትቅደም›› የሚባል አዲስ መፈክር በማንገብ፣ ‹‹የአሜሪካን ግዙ፣ አሜሪካዊያንን ቅጠሩ›› የሚል ዘመቻ ይዟል፡፡ ‹‹የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ለአሜሪካ ጥቅም ያልቆመ ነው›› ተብሎ አሜሪካ ከድርጅቱ እንድትወጣ አዲስ ሕግ መረቀቁ በራሱ የሚለው ብዙ አለው፡፡ የዓለምን የወደፊት አቅጣጫም ብዥታ ውስጥ ይከታል፡፡ የአውሮፓ ፅንፈኛ ቀኝ ፓርቲዎች የጀመሩት ኅብረቱን የመናድ ዘመቻ ሌላው አዲስ ክስተት ነው፡፡ በአካባቢያችን የሚሰሙት አዳዲስ የሥጋት ወሬዎች መጪውን ጊዜ አሳሳቢ ያደርጉታል፡፡ ይህንን ወቅት እንደ ዋዛ ማየትና መዘናጋት በራሱ አደጋ አለው፡፡ ከዚህ ሁሉ ይልቅ ታላቁን የኢትዮጵያዊነት ምሥል የጋራ አጀንዳ አድርጎ አንድ ላይ መቆም ለኢትዮጵያ አገራችን ይበጃታል፡፡ በአገር ጉዳይ የጋራ መግባባት በመፍጠር ለልዩነትና ለጥፋት የሚጋብዙ አጉል ድርጊቶችን ማስወገድ ይበጃል፡፡ ራስ ወዳድነት ለአገር አይጠቅምም፡፡ በመሆኑም ለአሳሳቢው የዓለም ተጨባጭ ሁኔታ የተጠናከረ አንድነት ያስፈልጋል!