ለ2009 ዓ.ም. የሚውል የ18.2 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ በጀት ፀደቀ፡፡ መንግሥት ያቀረበውን የተጨማሪ በጀት አዋጅ ፓርላማው በመጀመሪያ ንባብ ማክሰኞ ጥር 9 ቀን 2009 ዓ.ም. አፅድቆታል፡፡ በዚህም መሠረት የ2009 ዓ.ም. አጠቃላይ በጀት 229.2 ቢሊዮን ብር ሆኗል፡፡
የተጨማሪ በጀት ረቂቅ አዋጁን ይዘት ለምክር ቤቱ ያብራሩት የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ኤዴታው አቶ አማኑኤል አብርሃ ናቸው፡፡ አቶ አማኑኤል እንዳብራሩት፣ ተጨማሪ በጀቱ አስፈላጊ ከሆኑባቸው ምክንያቶች መካከል መንግሥት ከጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለመንግሥት ሠራተኞች ተግባራዊ የሚያደርገው የደመወዝ ጭማሪ በዋነኝነት ይገኝበታል፡፡
መንግሥት ከጥር 1 ቀን ጀምሮ ተግባራዊ ለማድረግ የወሰነው የደመወዝ ጭማሪ በአገር አቀፍ ደረጃ የመንግሥት ሠራተኞችን ተጠቃሚ ያደርጋል፡፡
ከክልሎችና ከፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ሚኒስቴር በተገኘው መረጃ መሠረት፣ ለደመወዝ ጭማሪው ዘጠኝ ቢሊዮን ብር መጠባበቂያ በጀት ያስፈልጋል፡፡
ከዚህም በላይ ተጨማሪ በጀቱ ለወጣቶች የተሻለ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታስቦ የተዘጋጀውን የተዘዋዋሪ ፈንድ ለማቋቋም ለሚያስፈልገው ወጪ የሚውል እንደሆነ አቶ አማኑኤል ገልጸዋል፡፡
ይኼንን ፈንድ ለማቋቋም አሥር ቢሊዮን ብር እንዲመደብ በመንግሥት መወሰኑንና ፈንዱን ለማቋቋም አዋጅ በመዘጋጀት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በቀሪዎቹ ስድስት ወራት የፈንዱን ሥራ ለማስጀመር የሚያስፈልገው ወጪ አምስት ቢሊዮን ብር በልዩ ልዩ ወጪዎች በጀት እንዲያዝ ሆኖ በተጨማሪ በጀቱ እንዲደገፍ ቀርቧል፡፡ ቀሪው አምስት ቢሊዮን ብር ደግሞ በ2010 በጀት ዓመት ለፈንዱ የሚከፈል መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል በ2009 ዓ.ም. በልማታዊ ሴፍቲኔት የተያዘው በጀት በቂ ሆኖ ባለመገኘቱ 1.5 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ በጀት፣ የድርቅ አደጋውን ለመከላከልና ቀሪ ግዴታዎችን በመወጣት አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት አንድ ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም ቀደም ሲል ተይዞ የነበረው መጠባበቂያ በጀት ሥራ ላይ በመዋሉ 1.41 ቢሊዮን ብር በመጠባበቂያ በጀትነት እንዲውል፣ ተጨማሪ በጀት ማፅደቅ አስፈላጊ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
በአጠቃላይ ለቀረበው 18.26 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ በጀት በገቢነት የተጠቀሰው ከነዳጅ ማረጋጊያ ፈንድ የሚገኘው ነው፡፡ በዚህም መሠረት 10.18 ቢሊዮን ብር ከነዳጅ ማረጋጊያ ፈንድ እንደሚገኝ፣ ከመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሽያጭ ገቢ ደግሞ 6.56 ቢሊዮን ብር እንደሚገኝ፣ እንዲሁም 1.23 ቢሊዮን ብር ከዘቀጠ ትርፍ (ከመንግሥት የልማት ድርጅቶችና ኢንቨስትመንቶች የሚገኝ የተጣራ የትርፍ ክፍያ) እንደሚገኝ ታሳቢ ተደርጓል፡፡
የነዳጅ ማረጋጊያ ፈንድ የመንግሥትን የበጀት ጉድለት በመሙላት ረገድ ትልቁን ሚና እየተጫወተ ሲሆን፣ አሁን ለቀረበው ተጨማሪ በጀት ትልቁ የገቢ ምንጭ ሆኖ ተጠቅሷል፡፡ በዚህም መሠረት የነዳጅ ማረጋጊያ ፈንድ የመንግሥትን የገቢ ፍላጎት በመሙላት ረገድ ለሦስተኛ ጊዜ ጥቅም ላይ ውሏል፡፡
የነዳጅ ማረጋጊያ ፈንድ በዓለም የነዳጅ ገበያ ዋጋና በብሔራዊ የነዳጅ ማከፋፊያ ዋጋ መካከል የሚገኝን ልዩነት የሚጠቅም ፈንድ ሲሆን፣ ዓላማውም የነዳጅ ዋጋ ለማረጋጋት የሚውል ነው፡፡ ፓላማው የቀረበለትን የበጀት ጥያቄ ከአስቸኳይነቱ አንፃር በመጀመሪያ ንባብ ተቀብሎ አፅድቆታል፡፡