ኢትዮጵያ ለጂቡቲ በነፃ የምትሰጠው የንፁህ ውኃ አቅርቦት ግንባታው ተጠናቆ፣ በሦስት ወራት ውስጥ ሙሉ በሙሉ ለጂቡቲያውያን መዳረስ እንደሚጀምር ተገለጸ፡፡
በጂቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሻሜቦ ፊታሞ ለጋዜጠኞች እንደገለጹት፣ በጂቡቲ መንግሥት ወጪ የተካሄደው የንፁህ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት ግንባታ አብዛኛው ሥራው ተጠናቋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የጂቡቲ ከተሞች በመጠኑ የውኃ ሥርጭቱ መጀመሩም ተጠቅሷል፡፡
በጂቡቲ የቀጣናው የኢኮኖሚ ትስስር ኮንፈርንስ ላይ ለመታደም ማክሰኞ ኅዳር 26 ቀን 2010 ዓ.ም. በጂቡቲ የተገኙት የትራንስፖርት ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሺዴ፣ ለመጪዎቹ መቶ ዓመታት የጂቡቲን የውኃ አቅርቦት ለማሟላት የሚያግዘው ፕሮጀክት በ350 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ሲገነባ ቆይቷል፡፡ የውኃው አቅርቦት በሶማሌ ክልል ሲቲ በተባለው አካባቢ በተካሄደ ቁፋሮ የለማ ሲሆን፣ እስከ ጂቡቲ በውኃ ማስተላለፊያ እንደሚሳብ አቶ አህመድ አስረድተዋል፡፡
ከውኃ በተጨማሪ በሦስት ኮሪደሮች በኩል እየተገነቡ የሚገኙ የመንገድ ፕሮጀክቶችንም ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል፡፡ ከአዲስ አበባ-አዋሽ-ሚሌ አድርጎ በጋላፊ በኩል የሚመጣው አንደኛው መንገድ ነው፡፡ ሁለተኛው ከድሬዳዋ-ደዋሌ የሚሄደው ሲሆን፣ ድሬዳዋን ከሚኤሶና ከአዋሽ መልሶ የሚያገናኘው መንገድ ግንባታ ነው፡፡ ሦስተኛው ከታጁራ ጋር የሚገናኘውና የኢትዮጵያን የፖታሽ ምርት ለማጓጓዝ የሚረዳው መንገድ በተለያዩ ኮንትራክቶች እየተገነባ እንደሚገኝ የጠቆሙት አቶ አህመድ፣ ከዚህ በተጨማሪ የጂቡቲን ወደብ ከጂግጂጋ ከተማ ጋር ለማገናኘት የሚረዳ የመንገድ ግንባታ ለማካሄድ ጥናት እየተካሄደ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
አምባሳደር ሻሜቦ እንደሚሉት በሁለቱ አገሮች መካከል እየተስፋፋ የሚገኘው የኢኮኖሚ፣ የንግድ፣ የሕዝብና የሌላውም ግንኙነት እየተጠናከረ ነው፡፡ ከሦስት ወራት በኋላ ኢትዮጵያ ለጂቡቲ የሰጠችው የንፁህ መጠጥ ውኃ አቅርቦት ግንባታው ተጠናቆ ሥርጭቱ እንደሚጀመር ይጠበቃል፡፡
እንደ አምባሳደር ሻሜቦ ገለጻ፣ ግንባታውን የጂቡቲ መንግሥት ሲያካሂድ የኢትዮጵያ መንግሥት ደግሞ ውኃውን በነፃ ያቀርባል፡፡