[ክቡር ሚኒስትሩ ከአማካሪያቸው ጋር ቢሮ እያወሩ ነው]
- እንዴት ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
- ሰላም ነህ?
- ዊኬንድ እንዴት ነበር?
- ይኼ የኳስ ነገር ሲበጠብጠኝ ነበር፡፡
- እርስዎም ተጎዱ እንዴ?
- ጉዳት ቢሉህ ጉዳት ነው፡፡
- እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
- እግር ኳስ ማለት እንደዚህ ነው እንዴ?
- ምንድነው የሚያወሩት ክቡር ሚኒስትር?
- ጨጓራዬ እንደዚሁ ሲላጥ ነበር፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እኔም እንደዚሁ ስቃጠል ነበር፡፡
- እግር ኳሱን እኮ ጦርነት ነው ያደረጉት፡፡
- እሱማ ተባሉ ማለት ይቻላል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እኔ ጨዋታው በሰላም የሚያልቅም አልመሰለኝም ነበር፡፡
- እግር ኳስ የሰላም መሆኑ እኮ የቀረ ነው የሚመስለው፡፡
- ለማንኛውም በጣም ነው የተቃጠልኩት፡፡
- እኔ ግን መንግሥት ትልቅ ዕርምጃ መውሰድ አለበት ባይ ነኝ፡፡
- መንግሥት? የምን መንግሥት?
- ይኸው ራስዎ የኳሱን ችግር እየነገሩኝ አይደል እንዴ?
- ልማታዊ መንግሥታችን እዚህ ሥራ ጠፍቶበት የእንግሊዝ ኳስ ውስጥ ይግባ እያልከኝ ነው?
- ምንድነው የሚያወሩት?
- ቅዳሜ አርሰናል 3ለ1 መሸነፉ እኮ ነው ያናደደኝ፡፡
- ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ አሉ፡፡
- ምን እያልክ ነው?
- እኔ የማወራው ስለአገራችን ኳስ እኮ ነው፡፡
- እዚህ አገር ኳስ አለ እንዴ?
- ለነገሩ ኳስ አለ ለማለት ይከብዳል፡፡
- ታዲያ ምንድነው የምታወራው?
- ለማንኛውም የአገሪቷ ኳስ የፖለቲካው መገለጫ እየሆነ ነው፡፡
- ኳስና ፖለቲካ ምን አገናኘው?
- እዚህ አገር ከተገናኙ ሰነባበቱ፡፡
- እንዴት ሆኖ ነው የተገናኙት?
- በአገሪቱ የሚታዩት ፅንፈኝነትና ክፍፍል በኳሱም እየተንፀባረቁ ናቸው፡፡
- የምን ክፍፍል ነው?
- ይኸው የኳስ ደጋፊዎችም በብሔር ተከፋፍለው እየተፋጩ ነው፡፡
- ስማ ማንኛውም ብሔር የእግር ኳስ ቡድን የማቋቋም መብት አለው፡፡
- ማቋቋማቸው አይደለም ችግሩ?
- ታዲያ ምንድነው ችግሩ?
- ደጋፊዎች በብሔር ተከፋፍለው እየተጋጩ ነው፡፡
- እ…
- ክቡር ማኒስትር ይኼ የብሔር ፖለቲካ በቃ ጦፎ ይኸው ኳሱ ላይ እየተንፀባረቀ ነው፡፡
- የምታወራው አልገባኝም፡፡
- ባንኩ በብሔር ነው፣ ቢራው በብሔር ነው፣ ቲቪው በብሔር ነው፣ ኳሱ በብሔር ነው፡፡
- እና ብሔር ብሔረሰቦች ይክሰሙ እያልክ ነው?
- እንደሱ አልወጣኝም፡፡
- ምን እያልክ ነው ታዲያ?
- አንድነታችንን ዘንግተን ልዩነታችን ላይ ካተኮርን በኋላ ዕጣ ፋንታችን መጠፋፋት ነው፡፡
- ዝም ብለህ ጨለምተኛ አትሁን፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ይኼ ያፈጀ ምክንያታችንን ትተን ለሕዝቡ ችግር በአፋጣኝ መፍትሔ ብናመጣ ይሻላል፡፡
- ምን ይፈጠር እያልክ ነው?
- የሰላምና የአንድነት መድረክ የሆነው እግር ኳስ ሳይቀር የብጥብጥና የጥላቻ መድረክ እየሆነ ነው፡፡
- ስማ ፖለቲካና ኳስ የተለያዩ መሆናቸውን አታውቅም?
- ክቡር ሚኒስትር ብጥብጡ እየተከሰተ ያለው ስታዲየም ውስጥ ሳይሆን ከዚያ ውጪ ነው፡፡
- መንግሥት ምን ያድርግ ታዲያ?
- ይኼ እኮ የፖለቲካ ሥርዓቱ ዝቅጠትን ማሳያ ነው፡፡
- አሁን በግልጽ እየዘለፍከን ነው፡፡
- እንዲያውም የፕሪምየር ሊጉ ስም አንደኛውን ቢቀየር ይሻላል፡፡
- ምን ይባል?
- የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ሊግ!
[የክቡር ሚኒስትሩ የእህት ልጅ ስልክ ይደውልላቸዋል]
- ሄሎ ጋሼ፡፡
- እንዴት ነህ ጎረምሳው?
- አለሁ ጋሼ፡፡
- ዛሬ ከየት ተገኘህ?
- አንድ ችግር ገጥሞኝ ነው፡፡
- ምን ሆንክ ደግሞ?
- ሰሞኑን መንግሥት ያወጣውን መግለጫ አልሰማህም?
- የትኛውን መግለጫ?
- ይኸው ራሳችሁን አጋልጡ እየተባለ ነው፡፡
- ሙሰኞችን ነው?
- በሌላ ቋንቋ ሙስኛ በለው፡፡
- ታዲያ አንተ የምን ሙስና ውስጥ ገብተህ ነው?
- ሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ያላችሁ ራሳችሁን አጋልጡ እየተባለ ነው፡፡
- አንተ ታዲያ ከዚህ ጋር ምን አገናኘህ?
- ረሳኸው እንዴ ጋሼ?
- ምኑን?
- አንተ እኮ ነው የገዛህልኝ፡፡
- ምኑን?
- ዲግሪዬን፡፡
- ምን?
- ቤት ለምን ትቀመጣለህ ስትለኝ ነጥብ አልመጣልኘም ስልህ አትጨነቅ ብለህ እኮ ነው የገዛህልኝ፡፡
- ለአንተ ነው እንዴ ያስመጣሁት? ለወንድምህ መስሎኝ?
- ለእሱም አስመጥተህለታል ጋሼ፡፡
- ታዲያ እሱ አልተጠየቀም?
- እሱማ ውጭ ስለሄደ ማን ይጠይቀዋል?
- ምን ላድርግልህ ታዲያ?
- እኔም እኮ ላማክርህ ነው የደወልኩት፡፡
- አሁን አንተን ጠይቀውሃል?
- መጠየቄ አይቀርም፣ ሰሞኑን ደግሞ ጥሩ ትምህርት አለህ ብለው አሳድገውኛል፡፡
- ማን ነው አንተን የሚጠይቅህ?
- የሰው ኃይል አስተዳደሩ ነዋ፡፡
- በቃ እደውልለታለሁ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ የሰው ኃይል አስተዳደሩ ጋ ደወሉ]
- ሄሎ ማን ልበል?
- ማን ልበል ይላል እንዴ?
- ይቅርታ ስላላወቅኩዎት ነው፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ነኝ፡፡
- በጣም ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር፣ ትንሽ ተበሳጭቼ ነው፡፡
- ምንድነው ያበሳጨህ?
- ሰሞኑን መንግሥት ያወጣው መግለጫ ትርምስ ፈጥሯል፡፡
- የትኛው መግለጫ?
- ይኼ ስለሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ የወጣው፡፡
- ለምን?
- እንዴ ይኸው በቃ ሁሉም ሠራተኞች ማለት ይቻላል ሐሰተኛ ማስረጃ ነው ያላቸው፡፡
- እ…
- እነዚህ ሠራተኞች ይባረሩ ቢባል በቃ ሥራ ማቆማችን አይቀርም፡፡
- ሥራማ እንዴት ይቆማል?
- ታዲያ ምን ማድረግ ይቻላል?
- በቃ ሠራተኞቹን መምከርና ከዛ ማስረጃቸውን እንደ ትክክለኛ ማስረጃ መቀበል ነው፡፡
- እንዴት ሆኖ?
- ምን የጨረቃ ቤቶች ራሳቸው ሕጋዊ ይሆናሉ አይደል እንዴ?
- ይኼማ ትልቅ ወንጀል ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ለማንኛውም እኔም የደወልኩልህ የእህቴ ልጅ ተመሳሳይ ችግር ገጥሞት ነው፡፡
- የምን ችግር ክቡር ሚኒስትር?
- እሱም ሐሰተኛ ማስረጃ ነው ያለው፡፡
- ምን እያሉኝ ነው ታዲያ?
- በቃ ምከሩት እያልኩ ነዋ፡፡
- ለማንኛውም ልጁ ግን ማን ነው?
- ሰሞኑን እንዲያውም ዕድገት የሰጣችሁት ኢንጂነር ነው፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እሱ እኮ የተሰጠው ኃላፊነት ትልቅ ተጠያቂነት ያለበት ነው፡፡
- ምን እያልክ ነው?
- አዲስ የሚገነባውን ግዙፍ ሕንፃ በአግባቡ መቆጣጠር ካልቻለ የሚያደርሰው አደጋ ከባድ ነዋ፡፡
- ምን እዚህ አገር የቀን ሠራተኛ ራሱ ሕንፃ የሚቆጣጠርበት አገር አይደል እንዴ?
- የእሱ ግን ከዚህም ያለፈ ነው፡፡
- ማለት?
- ልጁ የብቃት ማነስ ብቻ ሳይሆን ሌላ አደገኛ መስመር ውስጥ ገብቷል፡፡
- የምን መስመር ነው?
- እንዲያውም ልጁ ሲቪል ኢንጂነር አይደለም እየተባለ ነው፡፡
- ታዲያ ምንድነው የተማረው?
- የሙስና ኢንጂነሪንግ!
[ክቡር ሚኒስትሩ በግምገማ የወጣ የመንግሥትና የፓርቲ ባልደረባቸውን ሆስፒታል ያገኙታል]
- እንዴ ክቡር ሚኒስትር እዚህ ምን ያደርጋሉ?
- ሆስፒታል ቤቴ ከሆነ ሰነባበትኩ እኮ፡፡
- ምነው ክቡር ሚኒስትር?
- አሉ የሚባሉ በሽታዎች በጠቅላላ አሉብኝ፡፡
- በሞትኩት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ከጨጓራ ጀምረህ እስከ አስም፣ ደም ግፊትና ስኳር ተሸክሜ ነው የምኖረው፡፡
- አይዞኝ አይዞኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን አለፋህ የበሽታ ኢንዱስትሪ ፓርክ ሆኛለሁ ብልህ ይቀለኛል፡፡
- አይ ክቡር ሚኒስትር አሁንም ይቀልዳሉ አይደል?
- ስማ በሽታዬን ከማወቄ የተነሳ ለራሴ መድኃኒት የማዘው ራሴው ነኝ፡፡
- እንዴት?
- የፓርቲ ግምገማ ላይ ስቀመጥ የስኳር መድኃኒት ነው የምወስደው፡፡
- እሺ፡፡
- የመንግሥት ግምገማ ከሆነ የደም ግፊት ነው የምወስደው፡፡
- እሺ፡፡
- ከለጋሽ አገሮች ጋር ስንገናኝ ደግሞ አስሜ ይነሳብኛል፡፡
- ይገርማል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ከግሉ ዘርፍ ጋር ስገናኝ ደግሞ ጨጓራዬ ነው የሚላጠው፡፡
- እሺ፡፡
- ብቻ በአጠቃላይ በሽታዬን አውቀዋለሁ ለማለት ነው፡፡
- ታዲያ ለእርስዎ እኮ የክብር ዶክትሬት ሳይሆን ትክክለኛው ዶክትሬት ነበር የሚገባዎት፡፡
- ወድጄ አይደለም፡፡
- ሰሞኑን በየሚዲያው ስለእርስዎ የምንሰማው ምንድነው?
- ይኸው እኔም ተደናግጬ ቁጭ ብያለሁ፡፡
- ግምገማው ከባድ ነበር?
- ልባረር፣ ነፃ ልውጣ አላውቅም፤ አምባሳደር ልሁን አማካሪ የማውቀው ነገር የለም፡፡
- ይኼን ያህል አስጨነቅዎት?
- በፀሎት ላይ ነው ያለሁት፡፡
- ምን ነካዎት ክቡር ሚኒስትር?
- ምነው?
- እርስዎ አንድ ባለሰባት ፎቅ ሌላ ደግሞ ባለዘጠኝ ፎቅ አለዎት አይደል እንዴ?
- እሱማ አለኝ፡፡
- ታዲያ በቃኝ ብለው ለምን አያስቀጥሉትም?
- ምኑን? የታላቁ መሪ ራዕይን ነው?
- ኧረ ኢንቨስትመንቱን፡፡
- እንዲህ በቀላሉ አይለቁኝማ፡፡
- ምን ያደርጉኛል ብለው ነው?
- መቀጣጫ ሊያደርጉኝ ይችላሉ፡፡
- እንደዚያ ከሆነማ መግባት ነዋ፡፡
- የት? ገዳም ነው?
- ኧረ በፍጹም፡፡
- ታዲያ የት ነው የምገባው?
- ጫካ!