በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሽብርተኝነት የተፈረጀውን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ዓላማ በመቀበል፣ መንግሥትን በትጥቅ ትግል ለመለወጥ ተንቀሳቅሰዋል የተባሉ አድራሻቸው በኦሮሚያ ክልል የሆኑ 13 ግለሰቦች ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
ተከሳሾቹ በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች ላይ አባላትን በመመልመልና በሴል በማደራጀት ወታደራዊ ሥልጠና በመስጠት የሽብር ተግባር እንዲፈጽሙ ኦነግ የሰጣቸውን ተልዕኮ ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን፣ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ሸዋ፣ ምዕራብ አርሲና ባሌ ውስጥ ነዋሪ መሆናቸው የተገለጸው ተከሳሾች ሐጂ ሁሴን ቴሶ፣ ሸጊቱ ነገዬ፣ ዳማ ሸንዱ፣ ሁሴን አብዶ፣ ያሲን ሐጂ አብደላ፣ ኩርኩር ቡላ፣ ዳሪም ወሪቃ፣ ደቀባ ዋሪዬ፣ ዑመር ጃፋር፣ በሪሶ ቁፋ፣ ሡልጣን ደስታ፣ ሳሊያ በዳሶና ደስታ በሪሶ ይባላሉ፡፡
ተከሳሾቹ በባሌና አካባቢዎቹ አባላትን በመመልመል፣ ክላሽንኮቭ ጠመንጃዎችን እስከ 30,000 ብር ድረስ መግዛት እንደሚቻል ኬንያ ለሚኖር የሽብር ቡድኑ አመራር መረጃ ሲሰጡ እንደነበር ክሱ ይገልጻል፡፡ በአጠቃላይ ተከሳሾቹ የኦነግ አባል በመሆንና በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች በመዘዋወር አባላትን መመልመልና በማደራጀት የሽብር ድርጅቱን ዓላማ ለማሳካት ሲንቀሳቀሱ በመገኘታቸው በማሴር፣ በማነሳሳትና በሙከራ ወንጀል ክስ እንደ ተመሠረተባቸው የዓቃቤ ሕግ ክስ ያመለክታል፡፡