ከሞጆ ደረቅ ወደብ ንብረታቸውን የማያነሱ አስመጪዎችን ዝርዝር ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክና ለንግድ ሚኒስቴር እንደሚያስተላልፍ፣ ብሔራዊ የሎጂስቲክስ ዓቢይ (አመቻች) ኮሚቴ አስታወቀ፡፡
የብሔራዊ ኮሚቴው አባላት የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ኢንተርፕራይዝ ናቸው፡፡ ረቡዕ ኅዳር 5 ቀን 2009 ዓ.ም. በጋራ በሰጡት መግለጫ፣ የውጭ ምንዛሪ ወጥቶበት ከውጭ የሚገባ ንብረትን ያላግባብ በደረቅ ወደቦች ለረዥም ወራት የሚያስቀምጡ ባለሀብቶችን ዝርዝር ለሁለቱ ተቋማት እንደሚያስተላልፉ አስጠንቅቀዋል፡፡ ብሔራዊ ኮሚቴው ይህንን ለማድረግ የተገደደው አስመጪዎቹ ተገምግመው የንግድ ፈቃዳቸው መሰረዝ የሚገባቸውን ንግድ ሚኒስቴር እንዲሰርዝ፣ ብሔራዊ ባንክ ደግሞ የውጭ ምንዛሪ እንዳያገኙ እንዲያደርግ እንደሆነ የኮሚቴው አመራሮች ተናግረዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በሞጆ ደረቅ ወደብ 9,400 ዕቃ የያዙ ኮንቴይነሮች ተከማችተው እንደሚገኙ፣ ከዚህ ውስጥ 2,300 የሚሆኑት ከሁለት ወራት በላይ ያለፉባቸው መሆኑን፣ የኮሚቴው አባል የሆኑት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የጉምሩክ ዘርፍ ምክትል ዳይሬክተሩ አቶ ሞገስ ባልቻ ለጋዜጠኞች ገልጸዋል፡፡
እነዚህ 2,300 ኮንቴይነሮች የተሰጣቸውን የ60 ቀናት ጊዜ ያሳለፉ በመሆናቸው እስከ ታኅሳስ መጨረሻ የማያነሱ ከሆነ እንደሚወረሱና በጨረታ እንደሚሸጡ አቶ ሞገስ ተናግረዋል፡፡
እነዚህ 60 ቀናት ካለፈባቸው ኮንቴይነሮች አብዛኞቹ ማለትም 1,620 የሚሆኑት የባለሀብቶች ሲሆኑ፣ የተቀሩት የመንግሥት መሆናቸው ተገልጿል፡፡