Sunday, September 24, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናበአዲስ አበባ ካቢኔ ያልተጠበቀ መጠነኛ ሽግሽግ ተካሄደ

በአዲስ አበባ ካቢኔ ያልተጠበቀ መጠነኛ ሽግሽግ ተካሄደ

ቀን:

በአዲስ አበባ ከተማ ሥር የሰደደውን የመልካም አስተዳደር ዕጦትና የሙስና መንሰራፋት ለመፍታት መሠረታዊ የካቢኔ ሹም ሽር ይካሄዳል ተብሎ ቢጠበቅም፣ ካቢኔው መጠነኛና ያልተጠበቀ ሽግሽግ አካሂዷል፡፡

ቅዳሜ ታኅሳስ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. በተካሄደው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ስብሰባ፣ የካቢኔ አባል ከሆኑ 19 ቢሮ ኃላፊዎች ውስጥ ስድስቱ ሹም ሽር ሲደረግባቸው አዲስ ለተከፈቱ ሁለት መዋቅሮች ሹመት ተሰጥቷል፡፡

አብዛኛዎቹ ተሿሚዎች ቀደም ሲል በአስተዳደሩ ሥር ባሉ መሥሪያ ቤቶች ውስጥ ሲሠሩ የነበሩ ሲሆኑ፣ ሹም ሽር ይካሄድባቸዋል ተብለው ሲጠበቁ የነበሩ ሌሎች ቢሮዎች በዝምታ ታልፈዋል፡፡

መጠነኛውና ከተገመተው በታች የተካሄደው ሹም ሽር በአዲስ አበባ ከተማ ሠራተኞች ብቻ ሳይሆን፣ በአመራሮች ጭምር መነጋገሪያ መሆኑ ታይቷል፡፡ የምክር ቤት አባላትም የተወሰኑ ሹመቶችን ነቅፈዋል፡፡

ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አመራር ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በተሿሚዎች ብቃትና ሥነ ምግባር ላይ ውይይት አልተደረገም፡፡ የጥልቅ ተሃድሶ አፈጻጸምንም ጥያቄ ውስጥ የሚጥል ነው፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ ለምክር ቤቱ አቅርበው ያሾሟቸው ሰባት የቢሮ ኃላፊዎች ናቸው፡፡

ከእነዚህ ውስጥ ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ከተማ መሬት ልማትና ከተማ ማደስ ኤጀንሲ ሥራ አስኪያጅ፣ በጉለሌ ክፍለ ከተማ ደግሞ እስከ ሥራ አስፈጻሚ ድረስ የሠሩት አቶ ለዓለም ተሠራ ይገኙበታል፡፡ አቶ ለዓለም በአስተዳደሩ መዋቅር ውስጥ ለዓመታት የቆዩ ሲሆን፣ ከንቲባ ድሪባ የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አድርገው ሾመዋቸዋል፡፡

የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ በሥሩ ስድስት ዋና ዋና መሥሪያ ቤቶች ሲኖሩት፣ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች በከፍተኛ ደረጃ ቅሬታ ከሚያነሱባቸው ዘርፎች ውስጥ የመሬት ዘርፍ ግንባር ቀደሙ ነው፡፡

በእርግጥ የአዲስ አበባ ከተማ ማስተር ፕላን ዝግጅት በመጠናቀቁና ማስተር ፕላኑን ለማስፈጸም አዲስ የተቋቋመው ፕላን ኮሚሽን፣ ከመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ የተወሰኑ ኃላፊነቶችን ይጋራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በዚህ መሠረት በመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ላይ የነበሩ ጫናዎች ይቀንሳሉ ብለው እንደሚያምኑ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

የአዲስ አበባ ፕላን ኮሚሽን የተቋቋመ ሲሆን፣ ከንቲባ ድሪባ አቶ ማቴዎስ አስፋውን ሾመዋል፡፡ አቶ ማቴዎስ ከ1990 ዓ.ም. ጀምሮ በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ዝግጅቶች ውስጥ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳደሩ ኃላፊና ባለሙያ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡

ከእነዚህ በተጨማሪ ቀደም ሲል የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ ልዑልሰገድ ይፍሩ፣ ከዓመታት በኋላ ወደነበሩበት የጥቃቅንና አነስተኛ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሆነው በድጋሚ ተሹመዋል፡፡

እኚህ ኃላፊ ወደተነሱበት ቦታ በድጋሚ መመለሳቸው አግባብ አለመሆኑን የምክር ቤት አባላት በስብሰባው ላይ ተናግረዋል፡፡

ዶ/ር ሰለሞን ኪዳኔም ቀደም ሲል የአዲስ አበባ የትራንስፖርት ፕሮጀክቶች ማስተባበሪያ ኃላፊ ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን፣ ከንቲባ ድሪባ የመንገድና ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አድርገው ሾመዋቸዋል፡፡

አቶ ዘሩ ሰሙር ደግሞ ቀደም ሲል የቴክኒክ ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር የነበሩ ሲሆን፣ ኤጀንሲው በቢሮ ደረጃ ተደራጅቶ የካቢኔ አባል በመሆኑ የቢሮ ኃላፊ ሆነው ተሹመዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔን የተቀላቀሉት አዳዲሶቹ ተሿሚዎች ዶ/ር ጀማል ኡመርና አቶ መሐመድ አህመድ ናቸው፡፡ ዶ/ር ጀማል የኦሮሚያ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ የነበሩ ሲሆን፣ ከንቲባ ድሪባ የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ኃላፊ አድርገው ሾመዋቸዋል፡፡

አቶ መሐመድ ደግሞ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዚዳንት የነበሩ ሲሆን፣ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ተደርገው ተሹመዋል፡፡ ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ ዲላሞ ኦቶሬ የንግድ ቢሮ ኃላፊ ተደርገው ከትምህርት ወደ ንግድ ተዛውረዋል፡፡ 

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የቤት ባለንብረቶች የሚከፍሉትን ዓመታዊ የንብረት ታክስ የሚተምን ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጀ

በአዋጁ መሥፈርት መሠረት የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የንብረት ታክስ መጠን...

እንደ ንብረት ታክስ ያሉ ወጪን የሚያስከትሉ አዋጆች ከማኅበረሰብ ጋር ምክክርን ይሻሉ!

የመንግሥትን ገቢ በማሳደግ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳላቸው የሚታመኑት የተጨማሪ እሴት...

ለዓለምም ለኢትዮጵያም ሰላም እንታገል

በበቀለ ሹሜ ያለፉት ሁለት የዓለም ጦርነቶች በአያሌው የኃያል ነን ባይ...