በኦሮሚያ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛው ትክክለኛ ውሳኔ በሰጡበት የክርክር መዝገብ ፊርማቸውን በማስመሰል፣ የውሳኔውን ሐሳብ በመቀየርና ሐሰተኛ የመዝገብ ቁጥር በማስፈረም ሐሰተኛ የፍርድ ውሳኔ የሰጠ የሕግ ኦፊሰር፣ በ15 ዓመታት ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ተወሰነበት፡፡
መልካ ሹሜ የተባለው ፍርደኛ በወረዳ ፍርድ ቤት የሕግ ኦፊሰር ሆኖ ሲሠራ፣ በውርስ ይገባኛል ጥያቄ ክርክር ተደርጎበትና ውሳኔ ተሰጥቶበት የተዘጋን ፋይል በማውጣት ሐሰተኛ ውሳኔ መስጠቱ ተመልክቷል፡፡ ሚያዝያ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ውሳኔ ያረፈበትን የክስ መዝገብ በማውጣትና የመዝገብ ቁጥሩን በመለወጥ፣ ለሌላኛው ወገን (ለማይገባው) አካል እንደተወሰነለት አድርጎ ውሳኔውን መቀየሩ ተገልጿል፡፡
ኦፊሰሩ ተጠርጥሮ በሰኔ ወር 2007 ዓ.ም. ከተያዘ በኋላ ጉዳዩ ሲጣራ በሐሰተኛ ሰነድ ጉዳዩን ማጭበርበሩ የተደረሰበት ሲሆን፣ በኦሮሚያ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት የቀረበበትን የሰነድና የቴክኒክ ማስረጃ ማስተባበል እንዳልቻለም ተገልጿል፡፡ በመሆኑም የሕግ ኦፊሰሩ ፈጽሞ የተገኘው ወንጀል ከፍተኛ ሆኖ በመገኘቱ በ15 ዓመታት ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፎበታል፡፡