Thursday, June 8, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትር

 [ክቡር ሚኒስትሩ በጣም ተናደው የቤት ሠራተኛቸውን አስጠሯት]

  • አንቺ ምን ሆነሻል?
  • ምን ሆንኩ ጋሼ?
  • ለምንድን ነው ሸሚዜን ያልተኮሽው?
  • ሥራ ይዤ ነው ጋሼ?
  • ማታ አይደል እንዴ እንድትተኩሽው የነገርኩሽ?
  • እንጀራ ስጋግር ነበር፡፡
  • እና ምን ለብሼ ልሂድ?
  • አሁን እተኩስልዎታለሁ ጋሼ፡፡
  • በምንድን ነው የምትተኩሽው?
  • በካውያ ነዋ፡፡
  • የከሰል ካውያ አለን እንዴ?
  • ኧረ በኤሌክትሪክ ካውያ ነው የምተኩሰው፡፡
  • መብራት እኮ የለም፡፡
  • እነዚህ መብራት ኃይሎች ደግሞ ጀመራቸው፡፡
  • ያልተጠየቅሽውን አትቀባጥሪ፡፡
  • መቼ ነው እነሱ ግን የሚሻሻሉት?
  • ስለእነሱ አይመለከተኝም፡፡
  • እንዴት አይመለከትዎትም?
  • እኔ ምን አገባኝ?
  • እረሱት እንዴ ጋሼ?
  • ምኑን?
  • ሚኒስትር መሆንዎትን፡፡
  • እ…
  • ይኼ እኮ የመንግሥት ሥራ ነው፡፡
  • ምን እያልሽ ነው?
  • እኔ እኮ እርስዎ ሚኒስትር ሲሆኑ ተገላገልን ብዬ ነበር፡፡
  • ከምን?
  • ከዚህ መከራ ነዋ፡፡
  • ከየትኛው መከራ?
  • ዛሬ ፊልም ሊያመልጠኝ ነው ማለት ነው?
  • የምን ፊልም?
  • ዛራና ቻንድራ፡፡
  • አንቺ እሱ ነው የሚያስጨንቅሽ አይደል?
  • ስለሌላ ነገርማ እንዳልጨነቅ አዋጁ ከልክሎኛል፡፡
  • የትኛው አዋጅ?
  • ጋሼ እኔ ፖለቲካ አያስወሩኝ፡፡
  • የምን ፖለቲካ ነው?
  • ያመለጠኝን ፊልም በፌስቡክ እንኳን እንዳላይ እሱም ተዘግቷል፡፡
  • በፌስቡክ ፊልም ታያለሽ?
  • እኔማ እርስዎን ተስፋ አድርጌ ነበር፡፡
  • እንዴት?
  • ጋሼ እርስዎ ሚኒስትር ሲሆኑ ብዙ ነገር ጠብቄ ነበር፡፡
  • ማለት?
  • መብራት የሚጠፋብን አልመሰለኝም ነበር፡፡
  • ሌላስ?
  • ውኃም እናጣለን ብዬ አላስብም፡፡
  • እሺ፡፡
  • ጋሼ የአክስቴ ልጅ እኮ የቀድሞ ሚኒስትር ቤት ነው የምትሠራው፡፡
  • እና?
  • በቃ ዓረብ አገር ያሉ ዘመዶቻችን ጋ ስልክ እንደፈለግን ነበር የምንደውለው?
  • እ…
  • እዚህም እንደዛ ይሆናል ብዬ አስቤ ነበር፡፡
  • እንደዛ ብታደርጊ የሚከተልሽን ታውቂያለሽ፡፡
  • ምንድን ነው የሚከተለኝ?
  • ጣትሽን ነው የምቆርጠው፡፡
  • ጋሼ መቼም እኔ ላይ አይጨክኑም?
  • ነገርኩሽ ሴትዮ፡፡
  • እና ጋሼ ሌሎቹ ሚኒስትሮች ቤት የሚገኘው ጥቅም እዚህ አይገኝም እያሉኝ ነው?
  • እኔ እንደዚህ ዓይነት ነገር ውስጥ አልገባም፡፡
  • እኔ የምለው ጋሼ፡፡
  • ምንድን ነው?
  • ሰዎቹ እርስዎን አልተቀበሉዎትም እንዴ?
  • እንደ ምን?
  • እንደ ሚኒስትር!

[ክቡር ሚኒስትሩ ቢሮ ሲገቡ አማካሪያቸውን አስጠሩት]

  • አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አንዳንድ ነገሮች ላይ መወያየት አለብን፡፡
  • እሺ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ያው እኔ ብዙ ጊዜ ምርምሩ ላይ ነው የቆየሁት፡፡
  • አውቃለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እና እዚህ መሥሪያ ቤት ስላለው የአስተዳደር ሥራ ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡
  • ምን ልንገርዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • መሥሪያ ቤቱ ውስጥ ያለው ዋሻ ምንድን ነው?
  • የምን ዋሻ ነው?
  • መሥሪያ ቤቱ በየፍሎሩ በፓርቲሽን የተሠራ ዋሻ አለው፡፡
  • እ…
  • ለምንድን ነው ሁሉም በፓርቲሽን ተከፋፍሎ የራሱን ቢሮ የያዘው?
  • ያው…
  • አውቃለሁ ለምን እንደዛ እንደሆነ፡፡
  • ማለት?
  • ሁሉም ጉቦ መቀባበሉ እንዲመቸው ነው፡፡
  • እ…
  • የመሥሪያ ቤቱ ዋና ዓላማ ሕዝቡን ማገልገል አይደል እንዴ?
  • በሚገባ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ስለዚህ ለተገልጋዮች የሚመች ቢሮ ነው ሊኖረን የሚገባው፡፡
  • የሚመች ሲሉ?
  • በቃ ተገልጋዮች በየቢሮው መግባት ሳይጠበቅባቸው በአንድ ፍሎር ላይ ተገልግለው መሄድ አለባቸው፡፡
  • ምን እያሉ ነው?
  • ዋሻዎቹ መፍረስ አለባቸው፡፡
  • እ…
  • አዎ ሁሉም ፓርቲሽኖች ፈርሰው ልቅ ቢሮ ይሁን፡፡
  • እርስዎ ካሉ እሺ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እሱ ብቻ አይደለም፡፡
  • ሌላ ምን አለ?
  • ካሜራ መገጠም አለበት፡፡
  • እ…
  • እያንዳንዱ ሠራተኛ እንዴት አገልግሎት እንደሚሰጥ በካሜራ ይታያል፡፡
  • እንዳሉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ስለዚህ ጉቦ መቀባበልም ይቀራል ማለት ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ጉቦን ለማስቀረት ስንቱ ቦታ ካሜራ ይተከላል?
  • ሁሉም ቦታ፡፡
  • እሱማ አይቻልም፡፡
  • ለምን አይቻልም?
  • አብዛኛው ድርድር የሚካሄደው እኮ በየመጠጥ ቤቱና በየሆቴሉ ነው፡፡
  • እ…
  • እና ከቢሮ ውጪ በርካታ ድርድር ይደረጋል፡፡
  • ለእሱም ዘዴ ይፈለግለታል፡፡
  • እሺ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ብቻ አሁን በአስቸኳይ ፓርቲሽኑ ይፍረስ፡፡
  • በአስቸኳይማ መፍረስ አይችልም፡፡
  • ለምን?
  • ጨረታ መውጣት አለበት፡፡
  • የምን ጨረታ?
  • የማፍረስ!

[የቀድሞ ክቡር ሚኒስትር አዲሱ ሚኒስትር በመሥሪያ ቤቱ ውስጥ ሊያመጡ ያቀዱትን ለውጥ ሰምተው ስልክ ደወሉላቸው]

  • ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ሰላም ማን ልበል?
  • እንዴት ነው አዲሱ ሥራ?
  • ጥሩ ነው፣ ማን ልበል?
  • የቀድሞ ሚኒስትር ነኝ፡፡
  • እንዴት ነዎት የቀድሞ ክቡር ሚኒስትር?
  • በጣም ደህና ነኝ፡፡
  • ምን እያደረጉ ነው አሁን?
  • እኔማ ኢንቨስተር ልሁን ወይስ አምባሳደር በሚለው ሐሳብ ግራ እየተጋባሁ ነው፡፡
  • እ…
  • ኢንቨስተር ብሆን ጥሩ እንደምሠራ አውቃለሁ፡፡
  • እሺ፡፡
  • አምባሳደርም ብሆን ሁሉ ወጪዬ በመንግሥት ተችሎ ስለምኖር ለእኔ ዕረፍት ነው፡፡
  • እ…
  • ግን አምባሳደር ብሆን የኢንቨስተር ሥራዬን ሊጎዳው ይችላል ብዬ ስላሰብኩ ግራ ተጋብቻለሁ፡፡
  • በጣም ያሳዝናል፡፡
  • ምኑ ነው የሚያሳዝነው?
  • አሁንም ስለራስዎት ነው የሚያስቡት?
  • ታዲያ ስለማን ላስብ?
  • ከቦታዎት ያስነሳዎት እኮ ይኼ አስተሳሰብዎ ነው፡፡
  • እኔ ከቦታዬ ብነሳም መውደቂያዬን አሳምሬ ነው፡፡
  • እ…
  • መጀመሪያዬ መቀመጫዬን አለች ስንጀሮ ሲባል አልሰሙም?
  • አሁንም እንደዚህ ዓይነት የወረደ አስተሳሰብ ነው ያለዎት ማለት ነው?
  • ለማንኛውም አሁን የደወልኩት ልመክርዎት ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • የምን ምክር?
  • መሥሪያ ቤቱ ውስጥ ሊያመጡ ያሰቡትን ለውጥ ሰምቻለሁ፡፡
  • እና ምን ይሁን?
  • ብዙ ባይለፉ መልካም ነው፡፡
  • ለምን?
  • ፓርቲሽን በማፍረስ ለውጥ ማምጣት አይቻልም፡፡
  • እርሱን ለእኔ ተውት፡፡
  • እና እርስዎም ቢያስቡበት ጥሩ ነው፡፡
  • ምንድን ነው የማስብበት?
  • ሹመትዎን ይጠቀሙበት፡፡
  • የተሾምኩት ለእኔ ጥቅም አይደለም፡፡
  • ታዲያ ለማን ነው?
  • ለአገር!

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሾፌራቸው ጋር ወደ ቤት እየሄዱ ነው]

  • የደካከሙ ይመስላሉ ክቡር ሚኒስትር?
  • አዎን ትንሽ ደክሞኛል፡፡
  • ታላቁን ሩጫ ሮጡ እንዴ?
  • አይ አልሮጥኩም፡፡
  • ዊኬንድ ላይ ኳስ አዩ?
  • እኔ እንደዚህ ዓይነት ነገር አይመቸኝም፡፡
  • የቀድሞ ክቡር ሚኒስትር እኮ ኳስ ሕይወታቸው ነበር፡፡
  • እንዴት?
  • ስብሰባ አቋርጠው ራሱ ደውለው ውጤት ይጠይቁኝ ነበር፡፡
  • ለዚህ ነዋ ቤቱን እንደዚህ ያበሰበሱት፡፡
  • ለነገሩ እኔም አልወዳቸውም ነበር፡፡
  • ለምን?
  • ራስ ወዳድ ናቸው፡፡
  • ማለት?
  • ራሴ ብቻ በልቼ ልሙት ነው የሚሉት፡፡
  • አልገባኝም፡፡
  • ስንትና ስንት ደላላና ባለሀብት ነው ያገናኘኋቸው፡፡
  • እና፡፡
  • በቃ ይኼው ስንት ፎቅና ፋብሪካ ለራሳቸው ሠርተው፣ እኔ ጎጆ እንኳን የለኝም፡፡
  • እ…
  • መቼም ክቡር ሚኒስትር እርስዎ እንደ እሳቸው አይደሉም?
  • ማለት?
  • እርስዎም ተጠቅመው እኔን ይጠቅሙኛል፡፡
  • ምን?
  • በርካታ ደላላና ባለሀብት አውቃለሁ፡፡
  • እና?
  • የሚኒስትር ጥቅሙ ምን ሆነና?
  • እ…
  • ደመወዝዎት እኮ ትታወቃለች፡፡
  • ምን?
  • ቶሎ ብለው ፎቅዎትን ይሥሩ ግን…
  • ግን ምን?
  • እኔንም ያስቡኝ፡፡
  • አንተ መባረር አለብህ፡፡
  • እ…
  • ከእኔ ጋር መሥራት አትችልም፡፡
  • ምን አደረግኩ?
  • የእኔ ሾፌር መሆን አትችልም፡፡
  • የእርስዎስ ካልሆንኩ የእርሳቸው መሆን እችላለሁ፡፡
  • የማን?
  • የቀድሞው ክቡር ሚኒስትር!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

በኦሮሚያ ክልል በስድስት ከተሞች የተዋቀረውን ሸገር ከተማን የማደራጀት ሥራ ተጀመረ

በአዲስ አበባ ዙሪያ በሚገኙ ስድስት ከተሞች የተዋቀረው ሸገር ከተማን...

የኦሮሞን ሕዝብ ታሪክ አልባ በማድረግ ታሪክ አይሠራም

በኢተፋ ቀጀላ​​  ከዛሬ ሃምሳ ዓመት ወዲህ ከተፈጠሩት የኦሮሞ ድርጅቶች መካከል ከኢጭአት በስተቀር፣...

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው አሠራር ወጣ ያለውን ‹‹የወደፊት ግብይት›› ሥርዓት በይፋ አስጀመረ

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው የማገበያየት ተግባሩ ወጣ ያለና በኢትዮጵያ...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ከቀጣዩ ዓመት በጀት ውስጥ 281 ቢሊዮን ብሩ የበጀት ጉደለት ነው ተባለ

ለቀጣዩ በጀት ዓመት ከቀረበው 801.65 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ በጀት...

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው አሠራር ወጣ ያለውን ‹‹የወደፊት ግብይት›› ሥርዓት በይፋ አስጀመረ

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው የማገበያየት ተግባሩ ወጣ ያለና በኢትዮጵያ...

የባንክ ማቋቋሚያ መሥፈርት እንደሚጠነክር ሚኒስትሩ ተናገሩ

 ባንኮች ስለውህደት እንዲያስቡም መክረዋል በኢትዮጵያ ውስጥ ባንክ ለማቋቋም የሚያስፈልገው መሥፈርት...

ማን ይቻለን?

በጠዋት የተሳፈርንበት ታክሲ ውስጥ በተከፈተው ሬዲዮ፣ ‹‹ይኼኛው ተራራ ያን...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ አመሻሹን መኖሪያ ቤታቸው ሲደርሱ ባለቤታቸው በቴሌቪዥን የሚተላለፈው የማዕከላዊ ኮሚቴ ገለጻ እየተከታተሉ አገኟቸውና አጠገባቸው ተቀምጠው የደረሱበትን አብረው መከታተል እንደጀመሩ፣ ባለቤታቸው ቴሌቪዥኑን ትተው መጠየቅ...

እኔ ምለው? እሺ... አንቺ የምትይው? የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ አባላት እንዲያወሩ ወይም እንዲጠይቁ አይፈቀድም እንዴ? እንዴት ይከለከላል? ታዲያ ለምንድነው ፕሬዚዳንቱ ብቻ የሚያወሩት? እያወሩ አይደለም፣ ገለጻ እያደረጉ ነው። ቢሆንም አንድም አባል...

[ክቡር ሚኒስትሩ አምሽተው ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ‹‹ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ሕዝባችንን እናሻግራለን›› የሚለውን የቴሌቪዥን ዜና ተመልክተው ለብቻቸው ሲስቁ አገኟቸው]

ስልክ እያወራሽ ነበር እንዴ? ኧረ በጭራሽ... ምነው? ታዲያ ምንድነው ብቻሽን የሚያስቅሽ? አይ... በቴሌቪዥኑ የሚቀርበው ነገር ነዋ። ምንድነው? ድሮ ድሮ ዜና ለመስማት ነበር ቴሌቪዥን የምንከፍተው፡፡ አሁንስ? አሁንማ ቀልዱን ተያይዘውታል... አንተ ግን በደህናህ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ስልካቸው ጠራ። ደዋዩ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ኃላፊ እንደሆኑ ሲነገራቸው የስልኩን መነጋገሪያ ተቀበሉ]

ሃሎ፡፡ እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። አንተስ? አስተዳደሩስ? ሕጋዊ ሰውነታችን ተነጥቆ እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ክቡር ሚኒስትር? ለዚህ ጉዳይ እንደደወልክ ገምቻለሁ። ደብዳቤም እኮ ልከናል ክቡር ሚኒስትር፡፡ አዎ። ሁለት ደብዳቤዎች ደርሰውኛል።...