ባጭሩ ቢቢሲ የሚባለውና በዓለም አቀፍ ዜና አውታርነት የሚታወቀው ብሪቲሽ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በአማርኛ፣ በኦሮሚኛና በትግርኛ ቋንቋዎች የሬዲዮ ፕሮግራም ሥርጭት እንደሚጀምር አስታወቀ፡፡
ቢቢሲ በድረ ገጹ እንዳስታወቀው፣ በ11 አዳዲስ ቋንቋዎች የሚጀምረው የዜና አገልግሎት ከ‹‹1940ዎቹ ወዲህ›› ከተከሰቱት ዐበይት የማስፋፊያ ፕሮግራሞች አንዱ ነው፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ በጣቢያው ተደራሽ የሆኑት የአፍሪካና የእስያ ቋንቋዎች አማርኛ፣ አፋን ኦሮሞ፣ ትግርኛ፣ ኢግቦ፣ ዩሩባ፣ ፒዲን፣ ጉጃራቲ፣ ኮሪያን፣ ማራቲ፣ ፑንጃብ እና ቴሉጉ ናቸው፡፡ ሥርጭቱም በመጪው ጥር ወር እንደሚጀመር ይጠበቃል፡፡
አዲሶቹን ቋንቋዎች ጨምሮ በ40 ቋንቋዎች አገልግሎቱን ተደራሽ ያደረገው የቢቢሲ ዓለም አቀፍ የ100ኛ ዓመት ኢዮቤልዩን በሚያከብርበት እ.ኤ.አ. 2022 የአድማጮቹን ቁጥር ግማሽ ቢሊዮን ለማድረስ ማነጣጠሩንም ሳይገልጽ አላለፈም፡፡ ከኢትዮጵያ ቋንቋዎች መካከል እስካሁን በቢቢሲ የዜና ሥርጭት ውስጥ የሚገኘው ሶማሊኛ መሆኑ ይታወቃል፡፡
በውጭ አገር ከሚገኙ የተለያዩ ሚዲያዎች መካከል በኢትዮጵያ ቋንቋዎች የዜና ሥርጭት ከሚያስተላልፉት የአሜሪካ ድምፅ (ቮይስ ኦፍ አሜሪካ) በአማርኛ፣ ኦሮምኛና ትግርኛ፤ የጀርመን ድምፅ (ጆቼቬሌ) በአማርኛ፤ ቫቲካን ሬዲዮ በአማርኛና ትግርኛ ይገኙባቸዋል፡፡
ቀደም ባሉት ዘመናት የግብፅ (ካይሮ)፣ የሶማሊያ (ሞቃዲሾ)፣ የሶቭየት ኅብረት (ሞስኮ) ሬዲዮ ጣቢያዎች በአማርኛ ዜናና ልዩ ፕሮግራሞችን ያስተላልፉ እንደነበር ይታወሳል፡፡