የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) በመካከለኛ አመራሮቹ ላይ ሲያካሂድ በቆየው ግምገማ በክልሉ በተፈጠሩ ችግሮች መግባባት ላይ መድረሱን፣ ሒስና ግለሒስ በማድረግ ጥፋተኛ ሆነው በተገኙት ላይ ዕርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡
ከጥቅምት 25 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለስምንት ቀናት በተካሄደው ግምገማ፣ የመንግሥትን ሥልጣን የግል ኑሮን ለማሻሻል መጠቀም በዋናነት ከታዩ ችግሮች መካከል ጎልቶ ወጥቷል፡፡
ከአዲስ አበባ 80 ኪሎ ሜትር ላይ በምትገኘው አዳማ ከተማ በተካሄደው የመካከለኛ አመራሮች ግምገማ መዝጊያ ላይ የተገኙት የኦሕዴድ ምክትል ሊቀመንበርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፣ ከሰፊው ሕዝብ ጋር በቀጥታ የሚገናኙ መካከለኛ አመራሮች የግል ጥቅም ማስቀደም የሚያስከትለውን አደገኛ ውጤት በውል እንዲገነዘቡና ከማናቸውም የግል ጥቅም በፀዳ መንገድ መሥራት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
‹‹የበደልነውን ሕዝብ ለመካስ ቁርጠኛ መሆን አለብን፤›› በማለት ዶ/ር ወርቅነህ ተናግረዋል፡፡
በጂማ ከተማ ሲካሄድ የቆየውን የመካከለኛ አመራር ግምገማ ሲመሩ የቆዩት የኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ አባል አቶ አብዱልአዚዝ መሐመድ እንደተናገሩት፣ የሕዝቡን ሥልጣን ለግል ፍላጎትና ጥቅም ማዋል ከአሁን በኋላ የማይሞከር ነው፡፡ በተካሄደው ግምገማ በዚህ ጉዳይ ላይ ከመካከለኛ አመራሩ ጋር መግባባት ላይ መደረሱንም አቶ አብዱልአዚዝ ተናግረዋል፡፡
ኦሕዴድ ከከፍተኛ አመራሩ በመቀጠል በመካከለኛ አመራሩ ላይ ያካሄደው ግምገማ በኦሮሚያ ክልል ለተፈጠሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች ተጠያቂውን ለመለየት ረድቷል ተብሏል፡፡
‹‹በተለያዩ ከተሞች በተካሄዱ ግምገማዎችም የአቅም ማነስና የሥነ ምግባር ችግር ያለባቸውን አካላት የማጥራት ሥራ ተሠርቷል፤›› ሲሉ የክልሉ ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊና የካቢኔ አባል አቶ ፍቃዱ ተሰማ ገልጸዋል፡፡
አቶ ፍቃዱ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በተካሄደው ግምገማ ችግር ባለባቸው ላይ ዕርምጃ የሚወሰድ ሲሆን፣ የተቀሩትን አመራሮች በድጋሚ የማደራጀት ሥራ ይከናወናል፡፡
ኦሕዴድ ከመካከለኛ አመራሩ በተጨማሪ ከሰኞ ኅዳር 5 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ጀማሪ አመራሮችን እንደሚገመግም አስታውቋል፡፡ ከጀማሪ አመራሮች ጋር የሚካሄደው ግምገማ ሲጠናቀቅ ከሕዝቡ ጋር ውይይት እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡