ከተመሠረተ ከአንድ መቶ ሃያ ዓመታት በላይ ማስቆጠሩ የሚነገርለት የዓለም አቀፍ ኦሊምፒክ ኮሚቴ (አይኦሲ)፣ ለብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ መመደቡ ታወቀ፡፡ ከተጠቃሾቹ ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች አንዱ የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ መሆኑም ይታወቃል፡፡
የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ዳንኤል አበበ እንደገለጹት ከሆነ፣ የዓለም አቀፍ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ቅዳሜ ኅዳር 3 ቀን 2009 ዓ.ም. በሲዊዘርላንድ ሎዛን ከተማ ባደረገው መደበኛ ስብሰባ ለኦሊምፒክ ሶሊዳሪቲ እ.ኤ.አ. ከ2017 እስከ 2020 የሚቆይ ስትራቴጂክ ዕቅድን ይፋ አድርጓል፡፡ በዕቅዱ ለስፖርትና ለአትሌቶች ልማት የሚውል 509,285,000 ዶላር በላይ በጀት መመደቡም ታውቋል፡፡
የዘመናዊ ኦሊምፒክ መሥራች ፈረንሳዊው ባሮን ዲ ኩበርቲን እርስ በራሳቸው የተጠላለፉ ቀለማቸው ሰማያዊ፣ ጥቁር፣ ቀይ፣ ቢጫና አረንጓዴ መደባቸው ደግሞ ነጭ የሆነ አምስት የኦሊምፒክ ቀለበቶቹን ንድፍ በመሥራት፣ እ.ኤ.አ. በ1913 ድንገት ብቅ ማለታቸው መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ በወቅቱ ንድፉን ሠርተው ለሚቀርቧቸው ወዳጆቻቸው አሳይተው ከቀለበቶቹ ጀርባ ያሉትን እሴቶች ለማስጨበጥ ሲሞክሩ ብዙዎች እንደተሳለቁባቸው፣ ሆኖም ከመቶ ዓመታት በኋላ ግን እነዚያ ቀለበቶች ዓለም ላይ ተፅዕኗቸው ከፍ ብለዋል፡፡ የቀለበቶቹ ትርጉምም አምስቱን ክፍለ ዓለማት እንዲወክሉ መደረጉ እምነት አግኝቶ ዘልቋል፡፡
የዓለም ሕዝቦች ይህንኑ የኦሊምፒክ መርሕ ተቀብለው ከቆዳ ቀለም፣ ከዘር፣ ከሃይማኖትና ከፖለቲካ ገለልተኛ መሆኑ በሚነገርለት ስፖርት ተሳስረው እንዲዘልቁ የበኩሉን ድርሻ እንደተወጣና አይኦሲም አሁን ለሚገኝበት ደረጃ የጎላ ሚና መጫወቱ ይታወቃል፡፡
እንደ ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴ መግለጫ ከሆነ ከ2017 እስከ 2020 በታቀደው መሠረት ሥራ ላይ እንደሚውል የሚጠበቀው ይህ ገንዘብ፣ አይኦሲ ከ2013 እስከ 2016 ድረስ ይዞት ከነበረው በጀት 16 በመቶ ብልጫ አለው፡፡ ገንዘቡም በዓለም ላይ ያሉ የብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ልዩ ድጋፍ የሚሹ የብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች ማዕከል አድርጎ ቀመሩ ስለመሥራቱ ጭምር ተገልጿል፡፡
በዚሁ መሠረት በጀቱ በዋነኛነት ለአትሌቶች ልማት፣ ለአሠልጣኞች፣ ለስፖርት አመራሮች ሥልጠናና የኦሊምፒክ እሴቶች የሆኑትን፣ ማለትም መከባበር፣ ወዳጅነትና የላቀ ውጤታማነት በዓለም እንዲሰፍን ለብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች እንደሚከፋፈል ተነግሯል፡፡ የገንዘብ ድጋፍም የእያንዳንዱ አገር ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በሚያቀርበው የሥራ ዕቅድ (ፕሮፖዛል) መነሻ በማድረግ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ታውቋል፡፡