የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት የግል የትራንስፖርት ኩባንያዎች፣ በመልቲ ሞዳል ትራንስፖርት ሥርዓት እንዲሳተፉ ጥያቄ አቀረበ፡፡
የሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ከማሪታይም ባለሥልጣን ጋር በጋራ በመሆን ባደረጉት ጥናት፣ በጂቡቲ ወደብ ለበርካታ ቀናት ተከማችተው የሚቆዩ የአገሪቱ ንብረቶች በፍጥነት መነሳት አለባቸው፡፡ በኮንቴይነር ታሽገው ከሚቀርቡ ንብረቶች ውጪ ያሉ ሌሎች ዕቃዎችም በመልቲ ሞዳል ትራንስፖርት ሥርዓት ወደ አገር ውስጥ መግባት እንዳለበት ተስማምተዋል፡፡
በዚሁ መሠረት በማኅበር የተደራጁ የጭነት ትራንስፖርት ኩባንያዎች ከኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ጋር በመዋዋል ወደ መልቲ ሞዳል ትራንስፖርት ሥርዓት መግባት እንዲችሉ፣ የትራንስፖርት ሚኒስቴር ውሳኔ እንዲያሳልፍ ጥያቄ መቅረቡን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
ትራንስፖርት ሚኒስቴር ውሳኔውን በቅርቡ ያስተላልፋል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ይህንን ተከትሎም ወደ አገር የሚገቡ ተሽከርካሪዎች፣ የአርማታ ብረቶች፣ የካፒታል ፕሮጀክት ዕቃዎች (ማሽነሪዎች) በመልቲ ሞዳል የትራንስፖርት ሥርዓት እንዲጓጓዙ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የመልቲ ሞዳል ትራንስፖርት ሥርዓት ንብረቱ ከተገዛበት አገር ጀምሮ የተቀናጀ የባህርና የየብስ ትራንስፖርት በመስጠት ባለቤቱ ዘንድ ማድረስ የሚያስችል ሲሆን፣ ዕቃዎች በጂቡቲ ወደብ እንዳይቆዩ በማድረግ አገሪቱ ለወደብ ኪራይ የምታወጣውን ወጪ የሚቀንስ ነው፡፡
በኢትዮጵያ በደረቅ ወደቦች ንብረቶች በመከማቸታቸው መንግሥት በየዓመቱ ከሰባት እስከ አሥር ሚሊዮን ዶላር እንደሚያወጣ፣ በጂቡቲ ወደብ ደግሞ ከተጠቀሰው መጠን በብዙ እጥፍ እንደሚከፍል መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ይህንኑ ጉዳይ አስመልክቶ የዋና ኦዲተር ጽሕፈት ቤት ምርመራ አድርጎ ሪፖርት እንዲያቀርብ መታዘዙን መዘገባችን አይዘነጋም፡፡