በሞጆ ደረቅ ወደቦች ለረዥም ጊዜ የተከማቹ ኮንቴይነሮችን ባለቤቶቻቸው እንዲያነሱ ተደጋጋሚ ጥሪ አቅርቦባቸው ባለመነሳታቸው መንግሥት መውረስ ጀመረ፡፡
ከውጭ አገሮች ገብተው በሞጆ ደረቅ ወደብ የተከማቹ ከ8,100 በላይ ኮንቴይነሮችን በተመለከተ አስተዳደሩ የሰጠው የአሥር ቀናት ጊዜ ገደብ ረቡዕ ታኅሳስ 4 ቀን 2010 ዓ.ም. ተጠናቋል፡፡ አብዛኞቹ ምላሽ አለመስጠታቸውን የሞጆ ደረቅ ወደብ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አዲስ አየለ ዓርብ ታኅሳስ 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በጊዜ ገደቡ ውስጥ አስመጪዎች ያለባቸውን የመንግሥት ዕዳ ከፍለው እንዲያነሱ፣ ያልተነሱትን ደግሞ እንደሚወርስ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ነበር፡፡
በመጨረሻው ጥሪም ቢሆን ምላሽ ከሰጡት ውስጥ አብዛኞቹ የይራዘምልን ምክንያት አልባ ጥያቄ ማቅረባቸውን አቶ አዲስ ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን የጥቂቶቹ ጥያቄ ከባንክ ሰነድ ጋር የሚገናኝ በመሆኑ ጥያቄያቸው ተቀባይነት ሊኖረው እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
‹‹በጊዜ ገደቡ ውስጥ ከግማሽ በታች የሚሆኑት ምላሽ ይስጡ እንጂ፣ አብዛኞቹ የሚጠበቅባቸውን የመንግሥት ዕዳ ለመክፈል ባጋጠማቸው የገንዘብ እጥረት ምክንያት እንዲራዘም ጠይቀውናል፡፡ ነገር ግን ከሚገባው በላይ ጊዜ ተሰጥቷቸው ስለነበር ከዚህ በኋላ ዕቃዎችን ለመውረስ የመለየት ሥራ እያከናወንን ነው፤›› ብለዋል፡፡ እስካሁንም በተደረገው ዕቃዎችን የመለየት ሥራ ሊወረሱ የተወሰነባቸው ኮንቴይነሮች ከ800 እስከ 1,000 እንደሚደርሱ ጨምረው ገልጸዋል፡፡
የጥቂት ኮንቴይነሮች ጉዳይ ከባንክ ሰነድ አለመቅረብና መዘግየት ጋር የተገናኘ በመሆኑ፣ የአስመጪዎች ችግር ነው ተብሎ እንደማይወሰድና ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጥ መወሰኑን አቶ አዲስ ጠቁመዋል፡፡
እንዲወረሱ የተወሰነባቸው ነገር ግን ገና በመጣራት ላይ ያሉ ዕቃዎች በቅርቡ ጨረታ እንደሚወጣባቸውም አስረድተዋል፡፡ በደረቅ ወደብ ከተከማቹ 8,100 ኮንቴይነሮች ውስጥ የመንግሥት ድርጅቶች ንብረት የሆኑም እንዳሉ የገለጹት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ ከተቋማቱ ጋር በግንባር በየቢሮአቸው በመሄድ የማግባባት ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡